Saturday, December 22, 2012

ቅ/ሲኖዶስ የሠየመው የፓትርያሪክ አስመራጭ ኮሚቴ ዓለም አቀፍ ተቃውሞ ቀስቅሷል

ምንጭ፡- አዲስ አድማስ (http://www.addisadmassnews.com/) 
 

‹‹ዕርቀ ሰላሙ ይቅደም›› የሚሉ ጳጳሳት የሲኖዶሱን ውሳኔ አንቀበለውም ብለዋል
የላሊበላው ውዝግብ ወደ አላስፈላጊ ግጭት እንዳያመራ ተሰግቷል
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የስድስተኛውን ፓትርያሪክ ምርጫ ዝግጅት የሚመራና እስከ ጥር መጨረሻ ዕጩዎችን የሚያቀርብ አስመራጭ ኮሚቴ መሠየሙ በቤተ ክርስቲያኒቱ ካህናትና ምእመናን ዘንድ ዓለም አቀፍ ተቃውሞ መቀስቀሱ ተገለጸ። ‹‹የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ ያገባኛል›› በሚል መርሕ በዋናነት በማኅበራዊ ሚዲያዎችና ብሎጎች እየተገለጸ ያለው ይኸው ተቃውሞ፤ የቤተ ክርስቲያን ሰላምና አንድነት የሚረጋገጥበት የዕርቁ ጉባኤ ‹‹የአባቶች ጉዳይ ብቻ አይደለም፤ ምእመናኑን ያገለለ ሊኾን አይገባም›› በሚል የካህናቱና ምእመናኑ ድምፅ እንዲደመጥ የሚወተውት ነው፡፡
የቅ/ሲኖዶሱ አባላት የኾኑ ሊቃነ ጳጳሳትን ጭምር ያካተተው የዚህ ተቃውሞ መነሻ÷ የአስመራጭ ኮሚቴው መቋቋም በሀገር ውስጥ በሚኖሩትና በውጭ አገር በስደት በሚገኙት አባቶች መካከል ለሚካሄደው የዕርቀ ሰላም ውይይት መሰናክል ይኾናል በሚል ነው፡፡
የቅ/ሲኖዶሱ የዕርቀ ሰላም ልኡክ በመኾን ወደ አሜሪካ ከተጓዙትና በዳላስ ቴክሳስ ከኅዳር 26 - 30 ቀን 2005 ዓ.ም በሰላምና አንድነት ጉባኤ አመቻችነት በተካሄደው የዕርቀ ሰላም ውይይት ላይ የተሳተፉት የደቡብ ወሎ ሀ/ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አትናቴዎስ ከትናንት በስቲያ ምሽት ለአሜሪካ ድምፅ ሬዲዮ በሰጡት አስተያየት÷ ቅ/ሲኖዶሱ እንደላካቸውና በሰላሙ ጉዳይ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር እየተነጋገሩ ‹‹ስንዝር ያህል መራመዳቸውን›› ገልጸዋል፡፡ የዕርቀ ሰላም ልኡካኑ ይህን እያደረጉ ባለበት ኹኔታ ስለ ፓትርያሪክ ምርጫ መወያየትና አስመራጭ ኮሚቴ ማቋቋም ‹‹ኾኗል ብለን አናምንበትም፤ ኾኖ ከተገኘ ግን አንቀበለውም፤ እንቃወመዋለን›› ብለዋል - በቅ/ሲኖዶሱ ውሳኔ ቅር የተሰኙት ብፁዕ አቡነ አትናቴዎስ፡፡
በሰሜን አሜሪካ የዋሽንግተን ዲሲ እና ካሊፎርኒያ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል በበኩላቸው÷ የጥቅምት ቅ/ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የወሰነው የፓትርያሪክ ምርጫ ሕገ ደንብ ተዘጋጅቶ የአሁኑ ስብሰባ እንዲጠራ እንጂ አስመራጭ ኮሚቴ ማቋቋም አዲስ ሐሳብ መኾኑን ለሬዲዮው በሰጡት ቃለ ምልልስ ተናግረዋል፡፡ በጥር ወር አጋማሽ በካሊፎርኒያ ሎሳንጀለስ ቀጣይ የሰላም ጉባኤ ለማካሄድ ቀጠሮ መያዙን ያስታወሱት ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል፤ የኮሚቴው መቋቋም የዕርቁን ሂደት እንዳያበላሸው ስጋት እንዳላቸው በመግለጽ ቅ/ሲኖዶሱ ከዕርቀ ሰላም ጉባኤው በፊት ሰፋ ያለ ሥራ ከማከናወን እንዲከለከል አሳስበዋል፡፡
የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ምንጮች ለአዲስ አድማስ እንደገለጹት÷ ቅዱስ ሲኖዶስ የስድስተኛው ፓትርያሪክ አስመራጭ ኮሚቴ ባቋቋመበት ስብሰባ ላይ የተገኙ አንዳንድ ሊቃነ ጳጳሳት÷ ‹‹አስመራጭ ኮሚቴውን ከመሠየማችን በፊት ቢያንስ ወደ አሜሪካ የተጓዘው ልኡክ እስኪመለስ መታገሥና ሪፖርቱን መስማት አለብን›› በማለት የቅ/ሲኖዶሱን ውሳኔ ተቃውመዋል፡፡ የተቃውሞውን አቋም ለማስቀየርና በውሳኔው ቃለ ጉባኤ ላይ ለማስፈረም እንዲሁም ውሳኔው ለብዙኀን መገናኛ እንዲገለጽ ለማድረግ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱና ከመንግሥት ተወክለዋል የተባሉ ከፍተኛ ሓላፊዎች በተለይ በቅ/ሲኖዶሱ ዋና ጸሐፊ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል ላይ ጠንካራ ጫና በማድረግ ላይ እንደሚገኙ ምንጮቹ ለዝግጅት ክፍላችን ገልጸዋል፡፡
ቤተ ክርስቲያኒቱ በመንፈሳዊ ልዕልናዋ፣ ለትውልድ ባላት አርኣያነትና ለዓለም አቀፍ ሐዋርያዊ ተልእኮዋ መጠናከር ልታስቀድመው ከሚገባት የዕርቅና ሰላም አጀንዳ አንጻር ‹‹ከፓትርያሪክ ምርጫው በፊት አንድነቱ ይቅደም›› በሚል የተያዘው አቋም ‹‹መደገፍ ይኖርበታል›› የሚሉት ምንጮቹ÷ የሊቃነ ጳጳሳቱን አቋም ለማስቀየር የሚካሄደውን ርብርብ በጣልቃ ገብነት ነቅፈዋል፡፡ የዕርቀ ሰላም ልኡካኑ ሪፖርታቸውን ለማቅረብ ዘግይተዋል የሚሉ ሌሎች ወገኖች በአንጻሩ÷ አስመራጭ ኮሚቴ መቋቋሙ የዕርቀ ሰላሙን ሂደት ሊያደናቅፈው እንደማይችል በመጥቀስ የፓትርያሪክ ምርጫ ሂደቱ መቀጠል እንደሚገባው ይከራከራሉ፡፡
በዳላስ ቴክሳስ ለሦስተኛ ጊዜ በተዘጋጀው ጉባኤ አበው ላይ ከኢትዮጵያና ከሰሜን አሜሪካ ቅዱስ ሲኖዶስ በተሠየሙ የሰላም ልኡካን ኅዳር 30 ቀን 2005 ዓ.ም የወጣው ባለሰባት ነጥብ የጋራ መግለጫ÷ አራተኛው ፓትርያሪክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ ወደ ኢትዮጵያ ስለሚመለሱበት ኹኔታ ከሁለቱም ወገኖች የተሰጡ ምክንያቶች በዝርዝር ታይተውና ተጠንተው እየተመከረባቸው የመጨረሻ ውሳኔ እንዲያገኙ፤ የሰላሙ ጥረት ለፍጻሜ እስከሚደርስ ድረስ ሁለቱም ወገኖች ለሰላሙ መሰናክል የሚኾኑ ማናቸውንም ሥራዎች ከመሥራት ተቆጥበው ትዕግሥት እንዲያደርጉ፤ ከጥር 16 - 18 ቀን 2005 ዓ.ም በካሊፎርኒያ ሎሳንጀለስ ለሚካሄደው አራተኛው ዙር የዕርቀ ሰላም ውይይት የሰላምና አንድነት ጉባኤው ልኡካን ወደ ሁለቱም ወገኖች ተልከው የማግባባትና የማቀራረብ ሥራ እንዲሠሩ ከስምምነት ላይ መደረሱን ያመለክታል፡፡
ይኹንና ከታኅሣሥ 1 ቀን ጀምሮ ከሳምንት በላይ ሲካሄድ የቆየው የቅ/ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የፓትርያሪክ ምርጫ፣ ሕገ ደንብ አጽድቆ ምርጫውን የሚያስፈጽም 13 አባላት ያሉት አስመራጭ ኮሚቴ መሠየሙ ተገልጧል፡፡ የኮሚቴው አባላት ከቅ/ሲኖዶስ አባላት፣ ከጠቅላይ ቤተ ክህነቱ መምሪያዎች፣ ከታላላቅ ገዳማትና አድባራት፣ ከሰንበት ት/ቤቶች እና ከማኅበረ ቅዱሳን እንዲሁም ከታዋቂ ግለሰቦች የተውጣጡ ናቸው ተብሏል፡፡
በሌላ በኩል÷ በሰሜን ወሎ ሀ/ስብከት በደብረ ሮሃ ቅዱስ ላሊበላ ገዳም ከብልሹ አሠራርና ሙስና እንዲሁም እየተባባሰ ነው ከሚባለው የቅርሶች ጉዳት ጋር ተያይዞ÷ አስተዳደሩ ከካህናቱና ምእመናኑ ጋር የገባበት ያልተፈታ ውዝግብ ከቁጥጥር ውጭ ኾኖ ወደ አላስፈላጊ ግጭትና ደም መፋሰስ እንዳያመራ ታላቅ ስጋት እንዳላቸው የከተማው ምእመናን ገልጸዋል፡፡ በቁጥር ከአንድ ሺሕ በላይ በሚደርሱ የገዳሙ ካህናትና ምእመናን ፊርማ የተደገፈውን አቤቱታቸውን በአዲስ አበባ ተገኝተው በድጋሚ ለቅ/ሲኖዶስ ጽ/ቤት ያቀረቡት የምእመናኑ ተወካዮች÷ ከዐቃቤ መንበረ ፓትርያሪኩ ጋር መወያየታቸውን ገልጸዋል፡፡ ‹‹በርግጥ አንድ ሰው በአንድ ቦታ ለስምንት ዓመት መቀመጡ አግባብነት የለውም፤ እንጀራም ይሻግታል›› ያሉት ዐቃቤ መንበረ ፓትርያሪኩ፤ ከሀ/ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ጋር በመነጋገር መፍትሔ እንደሚሰጧቸው እንደነገሯቸው ምእመናኑ ለዝግጅት ክፍሉ አስታውቀዋል፡፡
በደብረ ሮሃ ቅዱስ ላሊበላ ገዳም በደማቅ ኹኔታ የሚከበረውና በቱሪስት መስሕብነቱ የሚታወቀው የገና (ቤዛ ኵሉ) እና የቅዱስ ላሊበላ ልደት በዓል በቀረበበት ኹኔታ በአስከፊ አስተዳደራዊ በደላቸውን መቀጠላቸው የሚነገርባቸው የገዳሙ አለቃ÷ አቤቱታ አቅራቢ ምእመናን እንዲታሰሩና እንዲንገላቱ ማድረጋቸውን፣ ካህናቱንና ምእመናኑን ከደመወዝና ከሥራ ማገዳቸውን እንደቀጠሉ መኾኑ ከከተማው ጸጥታ አንጻር ስጋት እንደሚፈጥር፣ ከሀ/ስብከቱና ከተማው አስተዳደር አቅም በላይ ኾኗል የተባለው ይኸው ጉዳይም በሰሜን ወሎ ዞን የፍትሕ፣ የፖሊስ እና የጸጥታ ጽ/ቤቶች እንደሚታወቅና በእነርሱም በኩል የክልሉ መንግሥት እንዲያውቀው መደረጉ ተመልክቷል፡፡

 

Thursday, December 20, 2012

የእግር እሳት - ወቅታዊ የቤተክርስቲያን ጉዳይ




ሰሞኑን ስለ ቤተክርስቲያን የተለያዩ ወሬዎች እየተሰሙ ነው፡፡ የሚነገሩት ነገሮች እውነት ከሆኑ የቤተክርስቲያን የመከራ ዘመናት ቢያንስ የሩብ መቶ ክ/ዘመን እንደተራዘመ ይሰማኛል፡፡ ቤተክርስቲያን በፖለቲካ መሪዎቻችን ተፅዕኖ ለሁለት ተከፍላ ሩብ መቶ ክ/ዘመን ስትበጠበጥ መንግስትም ሲፈልግ ልጆቿን ሲፈልግ ምዕመናኑን ሲያስፈልገው ደግሞ የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ካህናትና ዲያቆናትን የቤተክርስቲያኗን ልዕልና እየተዳፈረ ከቤተክርስቲያን አውድ ላይ እያፈሰ እየወሰደ ቢሻው ሲገድል፣ ቢያሻው ሲያስር፣ ሲፈልግ ደግሞ ሲገርፍ ኖሯል፡፡ ይህም ብቻ አይደለም፤ በአባ ጳውሎስ አማካኝነት እነ አለቃ አያሌውን የመሳሰሉ ሊቃውንት ከቤተክርስቲያን እየተወገዱ ሌሎች ሰሜንኛ ሰዎች ተተክተው ቤተክርስቲያንን መሸጫና መለወጫ፣ የሙስና ማቀናበሪያ፣ የዘረፋ ፕሮጀክቶች መንደፊያ፣ ማበልጸጊያ፣ መተግበሪያ ወዘተ በማድረግ  ቤተክርስቲያን የብልሹ አሰራር ምሳሌ፣ የዘረፋ ማዕከል፣ የዘረኝነት ፅንፍ ማዕረግ መሸለሚያ፣ የመንግስት አሻንጉሊት የሆነ ትውልድ መፈልፈያ፣ የጸረ-ተዋህዶ የእፉኝት ልጆች መፈልፈያ ወዘተ እንትሆን አድርጓል፡፡
ይህ ያሳለፍነው ሩብ መቶ ክ/ዘመን በአቶ ታምራት ላይኔ (የሀገሪቱን ሀብት በአጭር አመታት ለመዝረፍ ያለታከተ መራል አልባ ሰው) አማካኝነት መሆኑ ደግሞ የህሊና ቁስል ነው፡፡ ሰሞኑን በሪፖርተር ጋዜጣ በአቶ ታምራት ላይኔ ስም የተቀመጠ ስምንት ሚሊዮን ዶላር ከስዊስ ባንክ ለኢትዮጵያ ተመላሽ ተደረገ በማለት የተዘገበውን መመልከት የአቶ ታምራት ላይኔ ሞራል አልባ የሙታን አባል ስለመሆኑ መናገር ቅር የሚያሰኘው ያለ አይመስለኝም፡፡ የቁም ሙታን ታሪክ እንዲህ ይፃፍላቸዋልበነገራችን ላይ ምንዝር ከአለቃው ትዕዛዝ ሳይሰጠው በራሱ ተነሳሽነት ይህንን ትልቅ የታሪክ ክፍተት ለመፍጠር በኢትዮጵያ ሁኔታ ይነሳሳል ብየ አላስብም፡፡ በዚህም አቶ ታምራት ላይኔ የፊታዉራሪነቱን ቦታ ወሰደ እንጅ ከበስተጀርባ የአለቅዮው ትዕዛዝ አይኖርም ለማለት ይከብደኛል በኔ እይታ፡፡ ይህም ባዶ ቦታውን በተተኪው የኢህአዴግ ቀኝ እጅ እንዴት እንደተሞላ በማየት ከበስተጀርባ የነበሩትን ረጃጅም እጆች መገመት አያዳግትም ባይ ነኝ፡፡
አሁንም በቤተክርስቲያን ጉዳይ ጣልቃ ገብቶ የሰላም ውጥኑን ለማደፍረስ፣ የኢህአዴግ አሻንጉሊት ለመተካት የሚሰሩ የመንግስት አካላት ከታምራት ላይኔ በሞራላዊ ይዘታቸው (ልዕልናቸው) እጅጉን የዘቀጡ ናቸው እላለሁ፡፡ ምክንያቱም ታምራት ላይኔ ከበረሃ እንደመጣ እምነት ምንድነው፣ ሰላምስ ምንደናት የሚለውን ለመመለስና እርቅና ይቅርባይነት ምን ማለት እንደሆነ ያዉቃል ቢያውቅም ክብደታቸውን ይመዝናል ብዬ አላስብም፡፡ ያኔ በእርሱ አመለካከት የደርግ የሆነ ሁሉ መወገድ አለበት፣ ማሸነፍ ሁል ጊዜ በእርሱ እይታ በጦርና በኃይል እንደሆነ አድርጎ የሚገነዘብበት ጊዜ ነበር ለማለት እደፍራለሁ፡፡ ያሁኖቹ ግን በምርጫ ማሸነፍ፣ መሸነፍ፣ ሰላም፣ ልማት፣ ዕድገት፣ ነጻነት፣ መተካካት፣ ወዘተ የሚባሉ አዳዲስ ጽንሰ ሐሳቦችን ያወቁ፣ ሀገር በመምራት የሩብ መቶ ክ/ዘመን ልምድ ያካበቱ በመሆናቸው ቤተክርስቲያኗን እራሷን እንድታስተዳድር ነጻ ሊተዋት ይገባ ነበር፡፡ በዚህም አሁንም በቤተክርስቲያን ጉዳይ ጣልቃ እየገቡ ያሉ የመንግስት አካላት ሞራል አልባ ባዶ ቀፎዎች፣ የንብ መንጋ የሌላቸው፣ ንብ አናቢውም በልዩ ልዩ ማዕጠንት ያላጠነው ከሸረሪት ድር ነጻ ያልሆነ ዝንብና ቢራቦሮ የሚጠመድበት የሸረሪት ማኅደር ቀፎዎችን ይመስላሉ፡፡ በእውነትም በቤተክርስቲያን ጉዳይ ጣልቃ ከገቡ አስቤ ዋጋ ያጣሁባቸው ባዶ ቀፎዎች እነዚህ ናቸው፡፡
ባለፈው አንድ የሪፖርተር ጋዜጣ ላይ "አገርና ሕዝብን የሚጎዱ ይወገዱ" በሚል ርዕስ ባስነበበን ፅሑፍ በመንግስት መስሪያ ቤቶች ቅን አገልግሎት እንደጠፋ፣ መልካም አስተዳደር እንደጠፋ፣ የሕዝብ ሀብት በተሹዋሚዎች እንደሚዘረፍ፣ ጥቂቶች ባለሥልጣናት ብቻ በትክክል እንደሚሰሩ አትቷል፡፡ ይህ የማይካድ ሐቅ ነው፡፡ አቤቱታ የሚመልስ ፍርድ የሚያስተለካክል ጠፍቶ ሰው ተሰላችቶ አቤት ማለት ቢያቆም መንግስት የመልካም አስተዳደር መስፈን ነው ብሎ መሸወድ የለበትም ይላል ፅሑፉ፡፡ ይህንን በትክክል እኔ እስማማበታለሁ፡፡ ዝም ያልነው ጩኸታችንን የሚሰማን አጥተን ነው፡፡ ከዚህ እንደምንረዳው በአሁኑ ሰዓት የኢህአዴግ አመራር አካላት ማለትም የአሁኑ መንግስት ከፍተኛ ተሸዋሚዎች በሞራል ልዕልና፣ በሥነ ምግባር፣ በታታሪነት፣ በአድሎዋዊ አልባነት፣ በግልፀኝነት፣ በአጠቃላይ በግብረ ገብነት የመጨረሻው የዝቅጠት ደረጃ ላይ መድረሳቸው ይሰማኛል- በእኔ እይታ፡፡
እናም እነዚህ የመጨረሻው የዝቅጠት ደረጃ ላይ የደረሱ ሰዎች እነ ታምራት ላይኔ የሠሩትን የባዶነት ታሪክ ለመድገም ቢሯሯጡ አይገርመኝም፡፡ ነገር ግን የመንግስትን ፈርጣማ ክንድ ተንተርሰናል፣ መንግስት እንዲህና እንዲያ በሏል፣ መንግስት እንዲህ አስፈራርቶናል ወዘተ በማለት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላትን በማስበርገግ የሚፈልጉትን የረከሰ፣ የማሰነ፣ የነተበ አሰራር በቤተ ክርስቲያናችን ላይ ማስቀጠል የለባቸውም፡፡ እናም የሚከተሉትን ነጥቦች መከተል ይኖርብናል እላለሁ፡-


. ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት


የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት የሆኑ ጳጳሳት ጥቡአን መሆን ይጠበቅባቸዋል፡፡ የማንንም ማስፈራሪያና ማንገራገሪያ መፍራት የለባቸውም፡፡ ከ30 እስከ 55 የሚሆኑ ሊቃነ ጳጳሳት ባሉበት ቅዱስ ሲኖዶስ ውስጥ ከ8 የማይበልጡ የመንግስት አካላት ድጋፍ ያላቸው ጳጳሳት ይህንና ያንን አደረጉ ሲባል መስማት እጅግ ይዘገንናል፡፡ የምንኩስና ሕይወት ሞት ነው፡- በመኖርና በመሞት መካከል መሞት የተሻለ የሆነበት፡፡ ታዲያ ፍርሃት ከየት የመጣ ነው? እኛ ልጆቻችሁ ከጎናችሁ ነን፡፡ ለቤተክርስቲያን የሚበጃትን እንጅ ለጥቅመኛና ለሥልጣን ጥመኛ የመንግስት ሹማምንቶች  "የሚበጃቸውን" አትምረጡ፡፡ ለቤተክርስቲያን የማይበጃት ለእነርሱም አይበጃቸውምና!!


. ሌሎች የቤተክርስቲያን አመራር አካላትና አገልጋዮች

ሁሉም የቤተክርስቲያን አመራር አካላትና አገልጋዮች ትክክለኛው የቤተክርስቲያን የሚበጅ እርቀ ሰላሙ እንዲሳካ፣ መልካም የቤተክርስቲያን መሪ አባት እንዲመረጥ የየበኩላችንን ኃላፊነት ልንወጣ ያስፈልገናል፡፡ በፀሎት፣ ድምጻችንን በማሰማት፣ ሂስ በመስጠት፣ በመጠቆም፣ በመወያየት ወዘተ፡፡

. ምዕመናን

ሁላችን ምዕመናን ደግሞ በጸሎት፣ በውይይት፣ ሂስ በመስጠት፣ መረጃ በመስጠትና በመለዋወጥ፣ አስፈላጊውን እገዛ ሁሉ በማድረግ ለእርቀ ሰላሙም ሆነ ለቀጣይ መሪ ምርጫ የበኩላችንን ልንወጣ ያስፈልጋል፡፡ አላስፈላጊ አካላት በቤተክርስቲያኗ ታሪካዊ ጉዞ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ እንዳያሳርፉ መከላከልም ያስፈልገናል፡፡

. መንግስት

በመጀመሪያ ደረጃ ከቤተክርስቲያን ጉዳይ ላይ እጁን ያንሳልን፡፡ ከዚያ ከጥሎ አላስፈላጊ ግርግሮችን ነቅቶ ይጠብቅ፡፡ ሁለተኛው እንኳን እራሱ መንግስት ግርግር ካልፈጠረ አላሰፈላጊ ግርግር የሚኖር አይመስለኝም፡፡ መንግስት እንኳን በቤተክርስቲያን ጉዳይ ጣልቃ ገብቶ ቤተክርስቲያን በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ አወንታዊ ለውጥ እንድታመጣ ማስቻል ይቅርና የራሱን ተቋማዊ አደረጃጀት ግልፅነትና ተጠያቂነት ባለው አመራር፣ ዲሞክራሲያዊ በሆነ የመተካካት መርህ ተመርቶ የራሱን የፓርቲ መዋቅር ዘላቂና ፅኑዕ መሰረት እንዲኖረው ማድረግ እንኳን አለቻለም፡፡ መንግስት ደጋፊና ቲፎዞ ምልመላ በተሯሯጠበት በተለይም ከምርጫ 97 በኋላ ባከናወነው "የተሳካለት"በተባለ እንቅስቃሴ ዛሬ ዛሬ በአቋራጭ ጥቅምን ለማሳደድ ባቀዱ ሆዳቸው አምላካቸው የሆኑ ስድ አደጎችን ያልምንም መመልመያ መሥፈርት በማጋበስ ወደ ኃላፊነት ቦታ በማስገባቱ እነዚህ ሰዎች በሚያከናውኑት ዘረፋ፣ አስተዳደራዊ በደል፣ ስንፍና፣ ቸልተኝነት፣ ዘረኝነት፣ የወሮበላ ጥቅመኛ ቡድን ምስረታ በራሱ የመንግስት አካላትና በገዢው ፓርቲ ውስጥ "ተቀምጠው የሰቀሉት ቆሞ ለማውረድ ይቸግራል"የሚባለው ብሂል በኢህአዴግ ላይ ተፈጻሚ በሆነበት በዚህ ሰዓት ይህንን የነተበ፣ የተጎሳቆለ፣ ብልሹ አሰራር በቤተክርስቲያን ላይ ለመጫን ማሰቡ የታሪክ ስህተት ይመስለኛል - ለእራሱም የሚበጀው አይመስለኝም፡፡ ንቅ እሳተ ገሞራ ጥንቃቄ ይደረግበታል፤ ለዘመናት የተረሳ የተዳፈነ እሳተ ገሞራ ግን መቼ ይነሳል? የት አካባቢ ይፈነዳል? ወዘተ ጥያቄዎችን መመለስ ይከብዳል፡፡