Wednesday, June 1, 2011

ሰው በምድር ሲኖር ሊያተርፍ የሚያቅደው ምንድ ነው?

እነሆ እኔነቴ እና እኔ በየቀኑ በሚኖረን የህይወት ተቃርኖ ጊዜ ሁልዜ አንድ ጥያቄ በአእምሮዬ ይመጣል። ይኸውም ”ሰው በምድር ሲኖር ሊያተርፍ የሚያቅደው ምንድ ነው?‘ የሚል ነው። የማቅደው እና ያቀድኩትን ለማግኘት የማደርገው እየተለያየብኝ።

ሰው በህይወት ዘመኑ ለህይወቱ ጠቃሚ መሆኑን ለይቶ ያልተረዳውን ጠቃሚውንም ጐጅውንም እንዲኖረው ይመኛል፤ ይፀልያልም። ነገር ግን እነዚህን ሁሉ ነገሮች እንዲኖሩት የሚሻው ለምን እንደሆነ ሲጠየቅ የሚመልሰው መልስ ሁልጊዜ ይገርማል።
ለምሳሌ አንድ ሰው እጅግ ባለፀጋ ሌላው ደግሞ ፈላጭ ቆራጭ መሪ አንዱ ደግሞ እጅግ ሊቅ እና እርሱ የደረሰበት የእውቀት ደረጃ ሌላ የማይደርስበት እና የዓለም ህልውና በእርሱ ክሂሎት እና እውቀት ጥገኛ ወዘተርፈ ሊሆን ይችላል።
ለምን ይህንን እንዲኖርህ ወደድክ ተብሎ ሲጠየቅ በምድር ላይ ጤናማ ደስተኛ እና ምቾት ያለው ህይወት መኖር እንደሚፈልግ እና እነዚህ ነገሮች እርሱ ለእነዚህ ጉዳዮች ማሟያ እንደሚጠቀምባቸው ሳያቅማማ ይናገራል።
ነገር ግን የጤናማ ህይወት ምንጭ ምንድነው? ገንዘብ ነውን? ወይስ ፈላጭ ቆራጭነት ነውን? ወይስ እውቀት ነውን?
የደስታ ምንጭስ ወዴት ነው? ገንዘብ ደስታ ይሆናልን? ስልጣንስ ደስታ ሆይ ወደ እኔ ና! ይለው ዘንድ ይችላልን? ወይስ እውቀት ደስታን በፋብሪካ ሊያመርተው ይችላልን?
የምቾትስ መገኛ ምንድነው? ገንዘብ ወይስ አዛዥነት ወይስ እውቀት?
እነዚህ ደስታ፥ጤናማነት እና ምቾት ምንድናቸው? መገኛቸውስ ምንድነው?
ልዑል እግዚአብሔር ሰውን ሲፈጥር ሰባት ባህሪያት እንዲኖሩት አድርጎ ነው የፈጠረው። ” ወይቤ ፡ እግዚአብሔር ፡ ንግበር ፡ ሰብአ ፡ በአርአያነ ፡ ወበአምሳሊነ - እግዚአብሔርም፡አለ፦ሰውን፡በመልካችን፡እንደ፡ምሳሌአችን፡እንፍጠር ‘ ዘፍ. ፩፥፳፮ ተብሎ እንደተፃፈ።
አራት ባህሪያተ ሥጋ እና ሦስቱ ባህሪያተ ነፍስ አሉት። አራቱ ባህሪያተ ሥጋ እንስሳትን ሲያስመስሉት ሦስቱ ባህሪያተ ነፍስ ደግሞ ፈጣሪውን እግዚአብሔርን ያስመስለዋል። ስለዚህ ደስታ ጤናማነት እና ምቾትን ስናስብ ሰው ሁለት ዓይነት ደስታ ጤናማነት እና ምቾትን እናገኛለን። ስጋዊ እና ነፍሳዊ።
የሰው የማስታወስ እና የመናገር የማመዛዘን ችሎታ ከነፍስ ባህሪያት የተገኙ በመሆናቸው ስጋዊ ደስታ ጤናማነት እና ምቾት የስጋ ስሜቶች በመሆናቸው እነዚህ ሲጐድሉ ተመለሶ መጎሳቆሉ አይቀሬ ነው። ለምሳሌ አንድ ሰው በብርድ ጊዜ የብርድ መከላከያ እና ምቾት ያላቸው በውድ ዋጋ የተገዙ አልባሳትን ቢለብስ እና ከጥቂት ጊዜ በኋላ ቢራቆት ቀደም ብሎ የለበሰውን ልብስ በማስታወስ መፅናናት ይሳነዋል። ይህ ልብስ የፈጠረው ጊዜያዊ ስሜት ከልብሱ መውለቅ ጋር አብሮ ይጠፋል። ሌሎችም ቁሳዊ በሆኑ ነገሮች ለሰውነታችን የምናደርጋቸው ተግባራት ዘላለማዊ የሆነ ምቾት ደስታ እና ጤናማነት ሊፈጥሩልን አይቻላቸውም።
ሰው ከሌሎች እንስሳት ተለይቶ መናገር (ነባቢነት) ማመዛዘን (ልባዊነት) እና ዘላለማዊ ህይወት (ህያውነት) አለው። በእነዚህ በሦስቱ ባህሪያተ ነፍስ አምላኩ ይመስላል፤ በምድር በስባሽ ፈራሽም ሆኖ አይቀርም። ስለዚህ በእነዚህ በባህሪያተ ነፍሳችን ልንረዳው የምንችለው ነገር ሁሉ ዘላለማዊ ሀብታችን እና ትርፋችን ነው። እንግዲህ እውነተኛ ጤናማነት ደስተኝነት እና ምቾት ከየት ይገኛሉ የሚለውን መሰረታዊ ጥያቄ እነዚህን ነገሮች በባህሪያተ ነፍሳችን እንዴት መረዳት እና ለባህሪያተ ነፍሳችን ገንዘብ ማድረግ እንችላለን ወደሚል ጥያቄ መቀልበስ እንችላለን። ምክንያቱም በነፍስ ባህሪያት ልንገነዘበው እና ልናጣጥመው የምንችለው ነገር ለዘለቄታው አብሮን የሚኖር በመሆኑ ነው።
ለምሳሌ ደስተኝነትን እንመልከት። አንድ ሰው ደስታን በቁሳዊ ነገሮች በገንዘብ እና በመሳሰሉት ነገሮች ማግኘት አይችልም። ቢገኝም ስጋዊ ባህሪያችን ብቻ የሚያጣጥመው ያ አስገኚው ሲጠፋ አብሮ የሚጠፋ ጊዜያዊ ስሜት ብቻ ነው የሚሆነው። ነገር ግን አንድ ሰው በአእምሮው ውስጥ ደስታ እና እርካታን የሚፈጥረው መልካም ሀሳብን ለአእምሮው ሲመግበው ነው። መልካም ሀሳብ እና መልካም ሥራ የአእምሮ ምግቦች ናቸው። እነዚህ መልካም ሀሳቦች እና ሥራዎች የሚገኙት ደግሞ ለሰው ሁሉ ቅን እና ደግ በመሆን ነው። ቅንነት እና ደግነት ደግሞ ከፍቅር የሚመነጩ ናቸው። ለማይወደድ ሰው ቅን እና ደግ መሆን ከቶ ከባድ ነው።
አንድ ሰው ሁልጊዜ አብሮት የሚኖር የልብ መረጋጋት እና ደስታን ገንዘብ ለማድረግ ሰውን ሁሉ እንዲሁ መውደድ ነው። ጠላቱን እንደራሱ አድርጎ የሚወድ ልብ ደስታ ዘላለማዊ ነው። በራሱ ላይ ባለድል ነውና። ሰውን ሁሉ ለመውደድ እራስን ማሸነፍ ትህትናን መልመድ እና መንፈሳዊ አባቶቻችን ታሪክ እኛም እንደ አቅማችን መለማመድ ያስፈልገናል።
ሰው ለባዊ ፍጡር በመሆኑ ከራሱ ስህተት የተነሳ የሚመጣበትን የአእምሮው ትችት መሸሽ ከቶ አይቻለውም። እግዚአብሔር እኛን ለባዊ አድርጎ ሲፈጥረን አእምሮን ያህል ርቱዕ ዳኛ በላያችን ሾሞብናል። እናም በጨለማ ተጋርዶ በስውር መጥፎ ሥራ በመስራት ብዙ ሀብት ብናፈራ በሰዎች ላይም ግፍ ብናበዛ ከእግዚአብሔር እና ከአእምሯችን ልናመልጥ አይቻለንም። ስለሆነም ሞልቶ በተረፈው ቤታችን ብቸኛ ሐዘንተኛ እንሆናለን።
ሌሎች የህይወት እሴቶችም ከዚህ ተለይተው የሚታዩ አይደሉም። ለስጋ ብቻ የሚመች ነገር ግን ለባህሪያዊ ነፍሳችን የማይመች ስራ ብንሰራ ስጋ የተደረገለትን ሁሉ በአጭር ጊዜ ረስቶ ለነፍስ ወቀሳ አሳልፎ ይሰጠናል። ምቾትም ሆነ ጤናማነት ሁሉም ከልብ ይመነጫሉ። በጐ ሥራ በመስራት በልቡ ሀሴት የሞላ ሰው አስጨናቂ ጉዳይ የለበትም። ጭንቀት ከሌለበት ደግሞ ሙሉ ሰውነቱ ጤናማ ይሆናል። ጤናማ ሰውነት ደግሞ ሁልጊዜ ምቾት ይሰማዋል። ”እነደ ንፁህ ህሊና የሚመች ትራስ አይገኝም!‘ አይደል የሚሉት አበው። ምንም ጥርጥር የለውም፤ ውስጣዊ ሰላም ከአፍኣ (ውጫዊ) ምቾት እጅጉን ይበልጣል። ምክንያቱ ደግሞ አፍአዊ ደስታን በስጋችን ውስጣዊ ደስታችንን ደግሞ በልባችን (በነፍሳችን) እንገነዘበዋለንና ነው።
እንግዲህ አንባቢ ሆይ! በምድራዊ ህይወትህ/ሽ ደስታን ምቾትን ጤናማነት እና የህሊና እርካታን ለማትረፍ ካቀድህ/ሽ የሚከተሉትን መመሪያዎች ተግብር/ሪ፦
፩ኛ. ፈጣሪህ/ሽ እግዚአብሔርን ውደደው/ጂው፤ ባለህ/ሽ ጊዜ ሁሉ እርሱ የሰውን ልጅ ለማዳን ብሎ የከፈለውን መስዋእትነት እና ላንተ/ቺ ያለውን ፍቅር አስብ/ቢ። በዙሪያህ/ሽ ያሉት በህይወት እንድትኖር/ሪ ያደረጉህ/ሽ ነገሮች ሁሉ የእርሱ ሀብቶች ሲሆኑ ያለምንም ዋጋ እንደሰጠህ/ሽ አስታውስ/ሽ።
፪ኛ.ሰውን ሁሉ እንዱሁ ውደደው/ጂው፤ አንተ/ቺ ለሰው ስለምታደርገው/ጊው ውለታ እና በጎ ሥራ አቅድ/ጅ እንጅ የማንኛውንም ሰው ስጦታ ተስፋ አታድርግ/ጊ። ስጦታውን ሳታገኝ ብትቀር/ሪ የኑሮህ/ሽ ዋጋ ምንጭ የሆነውን ለዚያ ሰው ያለህን/ሽን ፍቅር ያቀዘቅዝብሃልና/ብሻልና። በምንም ዓይነት መንገድ ለራስህ/ሽ አታዳላ/ይ።
፫ኛ. ቁሳዊ ነገሮችን አብዝተህ/ሽ አትመኝ፤ ከማንኛውም ሰው ወይም ከፈጣሪህ/ሽ ይልቅ ለእነዚህ ቁሳዊ ነገሮች የበለጠ ፍቅር እንዳይኖርህ/ሽ እራስህን/ሽን በየጊዜው መርምር።
፬ኛ. ሁል ጊዜ አእምሮህን/ሽን በማይጠቅም ሐሳብ እንዳይባዝን እራስህን/ሽን በጸሎት እና በሥራ ባተሌ አድርግ/ጊ። በተግባር የሚለወጥ ሐሳባ ቢኖርህ/ሽ በእቅድህ/ሽ ውስጥ ፃፈው እንጅ በበጐ አስጀምሮ የተከተልከው/ሽው ሐሳብ መንታው እየበዛ ህልም ከሚመስል ቅዠት ውስጥ እንዳያስገባህ/ሽ የሞት እናት የሆነውንም ሐጢያት ጣዕም አጉልቶ እንዳያሳይህ/ሽ።
፭ኛ. መንፈሳዊነት እንደ ክሂሎት የሚዳብር ነው፤ እናም ተለማመደው/ጂው። ቁጣን ለማስወገድ፥ ትሁት እና ታጋሽ ለመሆን፥ የአፍህ/ሽ ቃላት ቅንነት እና መልካምነትን የሚያሰዩ ቁጣን የሚያበርዱ እንዲሆኑ፥ፍቅር እና ሌሎች የመንፈስ ፍሬዎች ገንዘብህ/ሽ እንዲሆኑ ተለማመድ/ጅ።
፮ኛ. ቅዱሳት መፃሕፍትን በየጊዜው አንብብ/ቢ፤ መልካም የሆነውን ሁሉ ለመረዳት ልብንም በሐይማኖት ለማቅናት ያስፈልጉሀልና/ሻልና። የዘነጋኸውን/ሽውን ለማስታወስ በቀዘቀዝክበት/ሽበት ነገር ለመነቃቃት ያገለግሉሃል/ሻል።
፯ኛ. ስንፍናን አስወግድ/ጅ፤ ለሥጋ ምግብነት የሚጠቅሙህ/ሽ እና በጐ ሥራ ለመስራት የሚያገለግሉህ/ሽ ነገሮችን ለማሟላት ተግተህ/ሽ ሥራ/ሪ። ነገር ግን ይህንን ምክንያት አስደርጐ የሚበልጥ ዋጋ እንዳያሳጣህ/ሽ ተጠንቀቅ/ቂ። ጸሎትህን/ሽን እንዳያታጉልብህ/ሽ፤ ከሌሎች ይልቅ ለራስህ/ሽ መድሎን እንዳያስደርግህ/ሽ፤ መልካም ሥራን እሰራለሁ አስብሎ መበደልን እንዳያስለምድህ/ሽ እራስህን/ሽን ጠብቀው/ቂው።
እንዲህ ያለ የፍቅር ህይወት ኖረህ/ሽ እየው/ይው። በህይወት ዘመንህ/ሽ ሁሉ ልታተርፈው/ፊው ያቀድኸውን/ሽውን ሁሉ ታገኛለህ/ሽ።

1 comment:

  1. በጣም ጥሩ ምክር አዘል ጽሑፍ ነው! እግዚአብሔር ይስጥልን! በሌሎች ርዕሰ ጉዳዮችም ተጠናክሮ ቢቀጥል መልካም ነው!

    ReplyDelete