Tuesday, August 2, 2011

የቤተክርቲያን የመከራ ዘመናት - ዛሬስ ሰላም ነውን? (ክፍል ሰባት)


በባለፈው ክፍል ስድስት ግራኝ አህመድ በሀገሪቱ እና በቤተክርስቲያን ላይ ያደረሰውን እልቂት እና ጥፋት ተመልክተናል። ዛሬ ደግሞ በዚህ ዘመን የደረሰው የጥፋት ዘመን አሉታዊ አሻራዎችን እንመለከታለን።
ባለፈው ክፍል እንደተመለከትነው ኦትማን ቱርኮች ኢትዮጵያን ልክ እነደሌሎቹ አጎራባች ሀረገራት ሁሉ የእስልምና መነሃሪያ ለማድረግ እና የምዕራብ አውሮፓ የክርስቲያን መንግስታትን በቀይ ባህር ላይ የሚያደርጉባትን ተቀናቃኝነት ለማስወገድ ኢትዮጵያን መቆጣጠር እና እስላማዊ መንግስት እንዲመሰረት ለማድረግ ግራኝን መርዳት እና ክርስቲያናዊ መንግስቱን መውጋት በእቅዱ ውስጥ በማስገባት በሀገሪቱ ላይ ከፍተኛ እልቂት እና ጥፋት ሊያስከትል ችሏል። በዚህ በ፲፭ ዓመት ጊዜ ውስጥ በቤተክርስቲያን እና በሀገሪቱ ላይ ያደረሳቸው ጥፋቶች የሚከተሉት ናቸው።
፩. የካህናት እና የቤተክርቲያን ሊቃውንት እልቂትበብዙ ሺህ የሚቆጠሩ እንቁ የቤተክርቲያን አባቶች ካህናት ዲያቆናት የቤተክርቲያን ሊቃውንት እና ገዳማውያን መነኮሳት ተጨፍጭፈዋል ታርደዋል አልቀዋል።
፪. የሕዝበ ክርቲያኑ እልቂት በግራኝ እና በሠራዊቱ ብዙ ንፁሐን ክርቲያኖች በሰይፍ ተሰይፈው በጦር ተወግተው እና እጅግ አሰቃቂ በሆነ አገዳደል የግፍ ፅዋ ጨልጠዋል። ብዙዎችም ተገደው ሰልመዋል። የእስልምና ተከታዮችን ተቀብላ በሰላም ያስተናገደች ሀገር እጇ አመድ አፋሽ ሆኖ በበጎ ፋንታ ክፉ ተመልሶላታል።  
፫. አቢያተ ክርቲያናት ገዳማት እና አድባራት መቃጠል በሺዎች የሚቆጠሩ አቢያተ ክርቲያናት ገዳማት እና አድባራት ተቃጥለዋል። እነዚህ ቦታዎች በዚያ ዘመን የሀገሪቱ የትምህርት  ማዕከላትም ስለነበሩ የነበራቸውን ልዕልና ይዘው መቀጠል ቢችሉ ኖሮ ሀገሪቱ ከፍተኛ የእድገት እመርታ ለማሳየት የሥነ እድገት እና የሥነ ልቦና ጥንካሬ ማዕከላት ሆነው የሀገሪቱ ዘመናዊነት መነሻ መካናት መሆን ይችሉ ነበር። ከዮዲት ጉዲት ዘመን በኋላ የተገነቡ አያሌ የትምህርት ማዕከላት ወደ ባድማነት ተቀይረዋል። የዘመናዊ ዩኒቨርሲቲዎች መመስረቻ መሆን ይችሉ ነበር። ፍፁም እግዚአብሔርን በመፍራት የተመሰረቱ የትምህርት ማዕከላት ስለነበሩ የሕዝቡ ሐይማኖታዊ ተነሳሺነት አይደበዝዝም ነበር።
፬. የመፃሕፍት እና ንዋያተ ቅድሳት መቃጠል አንቱ በተባሉ የቤተክርስቲያን ሊቃውንት የተፃፉ የሐይማኖት የፍልስፍና የሥነ-ህንፃ የሥነ-ጥበብ የዜማ እና የሥነ-መንግስት የሥነ-ህክምና የሥነ-ፈለክ እንዲሁም የሥነ-ልቦና መፃሕፍት ወደ አመድነት ተለውጠዋል።     

የግራኝ የጥፋት ዘመን በኋላ የዚህ ዘመን ያስከተለው የረጅም ጊዜ አሉታዊ አሻራዎች ክ/ዘመን ተሻጋሪ ከመሆናቸው የተነሳ ዛሬ ላለንበት የሀገሪቱ ኋላ ቀርነት እና የማንነት ማጣት ጥያቄ እንዲሁም የቤተክርስቲያን ዘርፈ ብዙ ችግሮች አይነተኛ መንስኤ ሆኖ በመቀጠል ላይ ነው። ይህ ዘመን ካስተላቸው የረጅም ጊዜ አሉታዊ አሻራዎች የሚከተሉትን መጥቀስ ይቻላል።
፩. የሐይማኖታዊ ባህሎቻችን መለወጥ በዮዲት ጉዲት ዘመን በነበረው የእልቂት ዘመን የባህል “አብዮት” ያላስከተለው የይሁዲዎች ክርስቲያናዊ ባህል ተፅዕኖ ውስጥ በመግባታቸው ልዩነቱን በሚገባ ጠንቅቀው ስላላወቁት እና በወቅቱ የነበረው የዮዲት ጉዲት ዘመቻም የታለመ ግብ ያለው ስላልነበር እንዲሁም የሀገራችን የክርስትና ሐይማኖት ከይሁዲነት የመጣ ስለነበር ኦሪታዊ የሐይማኖት ባህሉ ከይሁዲዎች ጋር ስለሚያመሳስለው ይህ የሐይማኖታዊ ባህል ለውጥ አሉታዊ ተፅዕኖ በሕዝቡ ላይ አላስከተለም ነበር።
ነገር ግን በግራኝ ወረራ ወቅት የተወረረው ክርስቲያናዊ ሕዝብ እና በወራሪው ሃይል መካከል የሰማይ እና የምድር ያህል የሚራራቅ ሐይማኖታዊ ባህል በመኖሩ በተወረሩት አካባቢዎች ሕዝቡ እንዲሰልም ከመገደዱም በላይ ሐይማኖታዊ ባህሉንም እርግፍ አድርጎ በመተው በዝሙታዊ የጋብቻ ሥነ-ስርዐት እና አሕዛባዊ የአኗኗር ዘይቤን እንዲለምድ በወራሪው ሃይል አማካኝነት ግዳጅ ስለተጣለበት ሐይማኖታዊ ባህሉ በመተው እንዝላል እና ግድ የለሽ እንዲሆን ተገዷል። የዚህ ግድ የለሽነት እና ሕዝቡ በአካባቢው ያሉት ቤተክርስቲያናት በመውደማቸው ምክንያት ያልተገባ አሕዛባዊ ፀባይ ውስጥ በመግባት ጣዖታትን ወደ ማምለክ እንዲሸጋገር በር ከፍቷል።
፪. የሐይማኖታዊ ትምህርቶቻችን ይዘት መቀነስ ወቅቱ ባደረሰው እልቂት ምክንያት የሐይማኖት ማመሳከሪያ የነበሩ መፃሕፍት እና ታላላቅ ሊቃውንት መሞት ምክንያት ለ፲፭ ዓመታት ያህል የነበረበትን አሕዛባዊ ልማድ ትቶ ተመልሶ ወደ እግዚአብሔር ለማቅረብ በነበረው ርብርብ መንፈሳዊ አገልግሎት ለተጠማው ሕዝብ የሚያገለግሉ እና የሚያስተምሩ የሚቀድሱ እና የሚያቆርቡ መምህራንን ካህናትንና ዲያቆናትን በአጭር ጊዜ ለማፍራት በማቀድ የቤተክርስቲያን አግልጋይነትን ለመሾም የሚጠይቀውን የመንፈሳዊ ብስለት እና የትምህርት ብቃት ስለተቀነሰ ቤተክርስቲያን የተጠበቀውን ያህል ለውጥ ማምጣት የሚችሉ የቤተክርቲያን ጠበቆች የሆኑ ሊቃውንትን ካህናትን እና አባቶችን ማግኘት አልተቻላትም።
ይህም ከዮዲት ጉዲት ዘመን በኋላ የነበረውን የመሰለ የቤተክርስቲያን ወርቃማ ዘመን እንዳይደገም እና ቤተክርስቲያንም ሆነ ሀገሪቱ ተመልሳ እንዳታንሰራራ ከፍተኛ አሉታዊ ተፅዕኖ አሳርፏል። ይህ አሉታዊ ተፅዕኖ በመጀመሪያ ቁጥር ፩ ላይ የተገለጸው አሉታዊ ተፅዕኖ ውጤትም ነበር።
፫. የአውሮፓውያን ሰባኪዎች መምጣት በወቅቱ የነበሩት ሃያላን የአውሮፓ ክርቲያን መንግስታት (ፖርቱጋል እና ስፔን) ከኢትዮጵያ በእስላማዊ ሀገራት ረዳትነት በእስላማዊ ሱልጣን ሀገሪቱ መወረሯን ተገልጾ እርዳታ ቢየጠየቁም በወቅቱ በቀይ ባህር ላይ የነበራቸውን ወደ ህንድ እና ወደ ሩቅ ምስራቅ የሚያደርጉትን የንግድ ጉዞ ተቃናቃኛቸው ኦትማን ቱርኮች መሆናቸውን ስለሚያውቁ በነገሩ ጣልቃ ላለመግባት እና ኦትማን ቱርኮችን ላለማስቀየም ይሁን ወይም ኢትዮጵያ ኦርቶዶክሳዊ ሀገር በመሆኗ የካቶሊክ ቤተ እምነት ተቀናቃኝ ተደርጋ ተወስዳ የርዳታ ጥያቄው ለ፲፭ ዓመታት ዘግይቶ ሕዝቡ ሁሉ አልቆ ብዙዎች ሰልመው ሀገሪቱ ሙሉ በሙሉ በእስላማዊ ሱልጣን ወታደሮች ተወርራ ታሪኳ ከተቀየረ በኋላ የፖርቱጋል ወታደሮች መጥተው በወይና ደጋ ጣና ሐይቅ አጠገብ በተደረገው ጦርነት ላይ ተሳትፈው አህመድ ገራኝ ስለተገደለ ድሉ በእነርሱ ምክንያት የመጣ አድርገው በመቁጠር በሀገሪቱ ላይ የራሳቸውን ዓላማ የሚያስፈፅሙበት እና ኦርቶዶክሳዊ ሐይማኖት ጠፍታ የሮማ ቤተ እምነት በኢትዮጵያ እንዲስፋፋ በማቀድ “መልእክተኞቻቸውን” ወደ ኢትዮጵያ በመላክ ባዕድ ትምህረት በማስተማር የእልቂት እና የጥፋት ዘመን ያሰቀቀውንና የሥነ-ልቦና ሰለባ ያጋጠመውን ሕዝብ ግራ ያጋቡት ጀመር። በሀገሪቱም ሁከት እና እልቂት እንዲነሳ በተለይ በአፄ ሱስንዮስ ዘመነ መንግስት ሐሳባቸው በንጉሱ ተቀባይነት ስላገኘ ከንጉሱ ወታደሮች ጋር በመሆን ሕዝቡን እንደጋና “ለማጥመቅ” ታቦታትን ከመንበራቸው ለማስወጣት የተለያዩ የቅዳሴ እና የቤተክርስቲያን ቀኖናዎች በሮማ ቤተ እምነት መሰረት እንዲከለሱ ለማድረግ በአጠቃላይ በቤተክርቲያን ላይ ዶግማዊ እና ቀኖናዊ እንዲሁም ትውፊታዊ ለውጥ ለማምጣት ሌት ተቀን ተግተው ከሦስት ቀናት ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ ከ፰ ሺህ ሰማእታትን ተሰይፈው እንዲገደሉ እና ምድሪቱ የእሪታ እና የእለቂት የሰቆቃ ምድር እንድትሆን አድርገዋል። በግራኝ ዘመን የደረሰበት ቁስል ሳያገግም በሕዝቡ ቁስል እና የሥነ-ልቦና ስብራት ላይ ሌላ ጥዝጣዜ እና የሞራል ውድቀት እንዲደርስ አድርገዋል። በዚህም ሀገሪቱ እየተዳከመች ሄዳ በመጨረሻ ከአንድ ክ/ዘመን በላይ የመከፋፈል እና የጦርነት ጊዜ የእርስ በእርስ ዝርፊያ እና ቅሚያ የበዛበት የመሳፍንት ዘመን እንድታስተናግድ ጥርጊያ መንገድ ከፍተዋል። ይህንን ታላቅ የምዕራባውያን በሰው ደም እና ህይወት ላይ የቁማር ጨዋታ ትውልድ ከታሪክ ማህደሩ በቀላሉ ሊፍቀው አይቻለውም። ዛሬም ይህንን እያስተናገድን ስለሆነ በዚያ ጊዜ የተከናወነው ግፍ ዛሬም እያየነው የትናንትናውንም የዛሬውንም ህመሙን እንድናዳምጥ እና እንዲሰማን ተገደናል።

…ይቀጥላል…

Sunday, July 24, 2011

WHY ORTHODOX FOR THE UNIFICATION OF AFRICA?

When this group was created, it was being thought to achieve the following two aims. These were:
1. To help the African people know the true way of Salivation that they never have been offered before. When you look into the rest of the world, it has been mad not to follow the true way of Salivation and intentionally left it behind and get into an other way of life which they termed Transformation in the fifteenth century (which bore the world of Protestantism) and so similar phenomena has happened in case of the fifth century (which bore the world of Catholics) i.e. (451 AD). But Africans have been forced or at least they have not been offered the true way of Salivation i.e. the religion of the Apostles that God Himself has handed over to them. We have also accepted the religion of our forefathers through unbroken flow of true religious exercises and tradition which is simply the true reflection of the Bible. So this pure truth should be at least offered to African people to whom no one else has offered before.
2. African people are getting very huge loses of its natural and man made resources due to the mischievous actions the western world and other developed countries. The boundary lines built up by the will of the colonial powers has left Africa in conflict with each other for centuries and this irritating condition may perpetuate for the coming centuries as well as we are looking it now. Not only the boundary lines but also other Economic, Political, Socio-Cultural and Psychological make ups that have been constructed by the European colonial powers has left its scar on the present deteriorated condition of Africa. I have pinpointed the only few past actions that made Africa the victims of the Western World. But not only the past action, at present days also, these developed world powers are acting as "mediators" over the African Issues and they are playing their negative roles on the developments of the good relations between Africans. They are influencing Africans not to have their own trade links and other strong relations to force Africa to be the indirect colonial empire of the developed world. If Africans could have unity, they would have got good opportunities to have an influencing power over the world about their own internal issue. They could get supplements of each other for the solution of a problem one region of Africa might be found at the other corner of the continent for example in natural resources and industrial and agricultural products. This in turn would produce an other ideal market for the products and resources of the continent. For unity to be effected the people at all should have one common identity and they should have one common ancient heritage. This ancient heritage should not be symbolic to inscribe the strongest sense of unity among the people. No other value or ancient heritage of Africa can bring life changing orders (life patterns) and heart felt senses inscription of unity better than religion. Religion is life at all. So it is preferred religion to any other Ancient Heritage for African people to have in common. Now let us come to the point how Orthodox should be the common Ancient Heritage of the African people. The following are some of the listed reasons that I have told to myself while I thought the concept of Unifying Africa:

A. Orthodox Religion was the most ancient religion of those religions having huge impact on the people of the world. It is simply practiced by the ancient Egyptians till today, Ethiopians till today, Libyans till they are affected by the Muslim world, and other North African Countries. This condition presents Orthodox Christianity the most ancient of all religions which have brought huge impacts on the lives of the population of the world.
B. Orthodox Christianity is established by the will of the African people without any power influences of the foreigners. When we look the Ethiopian Orthodox Tewahido Church establishment, it traces back to the ancient times more than 4000 years ago. Ethiopians were being knowing God as early as the man kind History and they were exercising worship of God before the Birth of Jesus Christ for about 2000 years. 1000 years without written commandments of God and 1000 years with given written laws of God. They have had the books of the Old Testament and they were waiting for the coming of Christ to Earth according their knowledge they have got from the Books of the Prophets and their Predictions. When Jesus Christ was born in the Middle East, they have gone to Him and brought Him Tributes and bowed to Him as stated in Isaiah:” And they from Sheba shall come: they shall bring forth gold and incense; and they shall show forth the praises of the Lord." They have accepted Him the True God and the true Son the Father. After 34 years later, a eunuch of great authority under Candace queen of the Ethiopians has gone to Jerusalem to worship and brought the news of Gospel to his fellow citizens. This was not the only beginning to worship God, but it was actually the beginning to the Era of Christianity in Ethiopia. But the greatest expansion of Gospel in Ethiopia could have been effected the fourth century. The people have accepted Christianity happily with their full will. When we come to Egypt, Saint Mark has left the base of the Gospel in Egypt and this flowing truth could have cross centuries and it has reached at our ages without being distorted and with living tradition of the first century of the Apostles. So only Orthodox Christianity is established by the full will of the African people and largely by their own actions to expand Gospel in the lands of Africa. But other religions are introduced to Africa forcefully by war having an other mission behind.

C. In the doctrines and canons of Orthodox Christianity true values of unity and sacrifice are preached under the Commandment of Love. The commandment of Love orders one to pay great scarifies up to and including giving up ones life for the sake of the other. The is the value to effect the true unity and heart felt Love to one another. It includes all the ethical values including the hard working traditions and avoidance of wickedness. These values coming following the commandment of Love are the true values that can bring these huge numbers of tribes under the common way of Unity and Shared common senses. In none of other religions these values are preached or at least practiced. But under Orthodox Christianity we have so many figures of Love and true mirror reflections of Gospel.

So now we are expected first to aim at valuing the African people by telling and helping them to know these pure facts. After this step, we can move forward to bring the whole Africa to get unified. The first is more difficult and also has to proceed first. So we will work visualizing the second one as well. So contents of the Spiritual and Religious Matters are to be posted for the group.

The issue of communication media language, we can use English. But since the present members of the group are Ethiopians and Amharic speakers, we can use also Amharic as a media language. Later when there are a number of other African Countries as members, we can use the language of the largest members additionally.

Other matters how we are going to proceed and related issues need to be defined by the group members using some discussion topics. We should strongly motivate group members to add values from their minds. The cumulative outputs outshine the individual outputs.

We have to strongly motivate other Africans to be members and active participants in our group. We should have diversified members to get the recent information and distributed effects.

These are some of the introduction that I thought for the time being. When I have some other things, I will notify you on time. You yourself can also broaden the starting idea into more meaningful proposals. But it does not urge you instantly. You can take long time and come up with more beautiful ideas. Our starting may be put into practice at the time the next generation, but we have to at least put the framework for having that.

God Bless African People!!!!

Wednesday, July 20, 2011

ሰው በምድር ሲኖር ሊያተርፍ የሚያቅደው ምንድ ነው? (ክፍል ሁለት)


በባለፈው ወር መጀመሪያ ላይ የዚህን ፅሑፍ መጀመሪያ ክፍል በዚህ መጦመሪያ ገፅ መነበቡ ይታወሳል። አሁን ካለፈው የሚቀጥል ሰው በምድር ሲኖር ሊኖሩት የሚመኛቸው እሴቶች በሚመለከት እንመለከታለን። የመጀመሪያውን ክፍል ለማንበብ እዚህ ይጫኑ!
 
ባለፈው ክፍል ለማየት እንደሞከርነው ሰው በምድራዊ ህይወቱ ጤናማ ህይወት፣ ደስታ፣ ፍቅር፣ ምቾት እንዲኖረው ይመኛል። የእነዚህ እሴቶች መገኛ ደግሞ ምን እንደሆነ በጥቂቱ ለመመልከት ሞክረናል። የሰው ልጅ ባህርይ ከእንስሳት ጋር የሚጋራቸው አራት ባህሪያተ ሥጋ እና ከእገዚአብሔር ጋር የሚያመሳስሉት ሦስት ባህሪያተ ነፍስ አሉት። እነዚህ ከላይ የተጠቀሱት እሴቶች ደግሞ ሰው በእንስሳዊ ባህሪው ሊያጣጥማቸው በሚችልበት ሁኔታ ብቻ ህይወቱን ከተረጎመው የሚያገኘው ደስታ እና ምቾት እንስሳት ጥሩ ምግብ በልተው በተደሰቱበት ጊዜ የሚያሳዩትን ፈንጠዚያ የሚመስል ይሆናል። እነዚህ እንስሳት ሆዳቸው በጎደለ ጊዜ ማጉረምረማቸው አይቀርም። ስሜታቸውም ለአጭር ጊዜ ብቻ የሚቆይ ነው። እናም ሰው ቁሳዊ በሆኑ ሀብቶቹ ለምሳሌ በገንዘብ በምግብ በልብስ እና በመሳሰሉት ነገሮች ሁሉ የሚያገኘው ደስታ ጊዜያዊ በመሆኑ ወዲያው ይጠፋል።
በአለም ላይ ያለውን ነባራዊ ሁኔታ ስንመለከት የሰው ልጅ ከእግዚአብሔር አምላኩ እፀ-በለስን በልቶ ከተለየበት ጊዜ አንስቶ ለስጋዊ ባህርይው የሚገዛ እና እውነተኛ ሰላምን በማጣቱ ከላይ የተጠቀሱት እሴቶችን ለዘለቄታው ለራሱ ማድረግ የተሳነው ሆኗል። ነገር ግን ብሩህ ተስፋ በክፉ ጊዜ ያለን መከራ የስቃይ ስሜት እንዲቀዘቅዝ ያደርጋልና ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማየ ሰማያት ወርዶ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማሪያም ተወልዶ በበደላችን ምክንያት የተረገመችውን ምድርን በኪደተ-እግሩ ቀድሶ ወንጌልን ለሕዝብ እና ለአሕዛብ አስተምሮ በጥምቀቱ በዮርዳኖስ በምድር የተቀበረውን የእዳ ደብዳቤያችንን ደምስሶ በቀናተኛ አሁዶች እጅ ተይዞ ተገርፎ እና መከራ መስቀልን ተቀብሎ በመስቀል ላይ ተሰቅሎ የእዳ ደብዳቤያችንን እና በደላችንን ሁሉ ደምስሶ እንደሚያድነን ለአዳም በሰጠው ተስፋ የሰው ልጅ ህይወት የደስታ ምንጮች የመዳን ተስፋ ሆነ።
በዚህ ብቻ አላበቃም ርህርሄው የበዛ አምላክ። የእግዚአብሔርን ትእዛዛት ብንጠብቅ በምድራዊ ህይወታችንም በባህሪያዊ ነፍሳችን የምንገነዘበው በህይወት ዘመናችን ሁሉ የሚያስደስተን የደስታ ምንጮችንም ከፈተልን። ከራሳችን ይልቅ ለሌሎች አድልተን ለእውነተኛ ደኛ ለሆነው አእምሮአችን የሚመች ሥራን በመሥራት ዘለቄታ ያለው ደስታ እና ምቾት ማግኘት እንደሚቻል ከተሰጠን ትእዛዛት እና ትእዛዛቱን በመጠበቃችን የምናገኘውን ሰማያዊ ዋጋ ብቻ ሳይሆን ምድራዊ ዋጋም ተነግሮናል።

ነገር ግን ከዘመነ አዳም ጀምሮ የተወሰኑ ሰዎች የእግዚአብሔርን ትእዛዛት በመጠበቅ መጀመሪያ በምድራዊ ህይወታቸው በኋላም በሰማያዊ ህይወታቸው የብዙ እሴቶች ባለቤት ሲሆኑ ሌሎቹ ግን እግዚአብሔርን በማሳዘን ትእዛዛቱንም በማፍረስ ቆየት ብለውም እርሱን በሌላ ባዕድ አምልኮ በመለወጥ ስላመነዘሩ የደስታ እና የሌሎቹ የህይወት እሴቶች ምንጮች ደረቁባቸው። አንዳንዶቹ በመቅሰፍት ሲያልቁ ሌሎቹ ደግሞ በምድር ላይ ተቅበዝባ ሆነው ህይወታቸውን ደስታን በማጣት ተጎሳቁለዋል።
ይህ ሁኔታ እየቀጠለ ሄዶ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአዳም የገባውን ቃል ለመፈፀም ወደ ዚህ ምደር በመጣ ጊዜ ዓለም የደስታ ምንጭ ምን እንደሆነ ግራ በተጋባ እና ደስታን ለማግኘት የደስታ መገኛ መንገዶች ተቃራኒ ሥራዎችን የሚሰራበት ጊዜ ነበር። እንኳን እግዚአብሔርን የማያውቁት አሕዛብ ይቅርና የእግዚአብሔር ሕዝብ የሚባሉት እስራኤል እንኳ ትክክለኛ የህይወት መስመርን ስተው የመሲህን አመጣጥ ከሮማውያን ቅኝ አገዛዝ ነፃ ከመውጣታቸው ጋር አያይዘው በተሳሳተ መንገድ ተስፋ አድርገው ነበር። ከዚህም በተጨማሪ እነዚህ ቤተእስራኤላውያን በሰው ፊት ብቻ የእግዚአብሔርን ትእዛዛት የሚጠብቁ ነገር ግን በስውር ሐጢያትን የሚፈፅሙ አስነዋሪ ስራዎችን የሚያደርጉ የተተበተቡ ትእዛዛትን በሌላው ላይ የሚጭኑ እነርሱ ግን በጣታቸው እንኳ ሊነኩት የማይፈልጉ በእግዚአብሔር ላይ አመፀኞች ነበሩ። ከዚህ እንደምንረዳው በዚህ ወቅት ዓለም የደስታ እና የፍቅር የምቾት እና የጤናማ ህይወት መስመሩን ስቶ አሰቃቂ የመገዳደል ወንጀል በበዛበት እና የነፍስ እረፍቷ የሚሆን ሥራ የተመናመነበት ጊዜ እንደነበር ነው። በሮማ ግዛት እና በሌሎች የጣዖት አምልኮ በነበረባቸው የአሕዛብ ነገስታት አገርም ደስታ የሚገኘው የተለያዩ ትርኢቶችን በመመልከት እንደሆነ ይገመት ነበር። በዚህም ምክንያት በተለያየ ምክንያት ወንጀለኛ ናቸው ተብለው የተያዙ እስረኞች በሞት እንዲቀጡ በመወሰን ከአናብስት እና ከአናምርት ጋር በአደባባይ በማታገል ነገስታቱ እና ሹማምንቱ እንዲሁም መኳንንቱ ይህን በመሰለው ትርኢት ደስታን ለማገኘት እና ለመዝናናት ይሞክሩ የነበረበት ዘመን ነዉ። ይህ አሰቃቂ የሆነ የሰው ልጆች ሰቅጣጭ ጩኸት ትርኢቱን ለመመልከት የሚመጣውን ሕዝብ አእምሮ ውስጥ የህልውና ጥያቄ የሚያስነሳ እና ህይወታቸው ቀጣይነቱን ለማረጋገጥ ዋስትና የሌለበት ዘመን ሆኖ ነበር። በሌላ በኩል ደግሞ በገው በኩልም ይህ ለአእምሮ የማይመች ሥራቸው የህልም ቅት እና ሰቆቃ እንጅ ደስታ እና ጤናማ ስሜትን ሊተርፍላቸው አልቻለም።

እንግዲህ አምላካችን ክርስቶስ የተወለደው በዚህ በተዘበራረቀ ዓለም ትክክለኛ የህይወት መስመር ውሉ የጠፋበት ዓለም እና ጊዜ ነው። የህይወት ጣዕም ጠፍቶበት ዓለም ወደ አልጫነት ተቀይሮ ነበር። በዚህ ጊዜ ከቅድስት ድንግል ማሪያም የተወለደው አካላዊ ቃል ይህንን የዓለም አልጫነት አስወግዶ የሚጣፍጥ ጨው ሆኖ ወደ ጣፋጭነት ቀየረው። ተስፋ የቆረጡ እና “ህይወት ምንድነው?” እስከ ማለት የደረሱ ድውያንን በተአምራቱ ርሁባነ ነፍሳትን በትምህርተ ወንጌሉ በማስተማር ዳግም ሰው የሞት ተሸናፊ አለመሆኑን ከሞት በኋላ ህይወት ያለ መሆኑን እና በትንሳኤ ዘጉባኤ ሞትን ድል ነስተን እንደምንነሳ በማስተማር ሰውን ዳግመኛ ወደ ፀጋ መንፈስ ቅዱስ ልጅነት መለሰው። በኦሪት የተሰጠች ትእዛዝን በማፅናት የፍቅር ትእዛዛትን ለሰው ልጆች የእውነተኛ እና ዘላለማዊ የህይወት እሴቶች መገኛ አድርጐ ከፊት ይልቅ በሐዲስ አፅንቶ ሰጠን። ሰው ሁለት ዓይነት ፍቅር ሲኖረው የመጀመሪያው ሰው ለፈጣሪው ለእግዚአብሔር የሚኖረው ከራሱ የበለጠ ፍቅር ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ሰው እርሱን ለመሰለ ሌላ ሰው የሚኖረው ፍቅር ከራሱ ፍቅር ጋር የተካከለ ነው። ነገር ግን ሁላችንም ልንገነዘበው የሚገባን ነገር እግዚአብሔር አነዚህን ሁለቱን የፍቅር ትእዛዛት ሲሰጠን የመጀመሪያው ፍቅር በሁለተኛው እንዲገለጥ ፈቃዱ ስለሆነ ሰው ሁሉ ለተቸገረ እና እርዳታ ለሚያስፈልገው ሁሉ የሚያናደርገው በጐ ሥራ ሁሉ ለእርሱ እንደተደረገ ሆኖ እንደሚቆጠር በስድስቱ ቃላተ ወንጌል ገልጦልናል።

በዚህም ነፍስንም ስጋንም የፈጠረ እግዚአብሔር የህይወት እሴቶችን ከትእዛዛቱ ጋር የተቆራኙ አድርጐ ለራሳችን በምንም ዓይነት መስፈርት እንዳናደላ አእምሮን ያህለ ርቱዕ ዳኛ በላያችን ሾሞ የነፍሳችን ማረፊያ የሚሆን ትእዛዛቱን በመፈፀም ደስታ ፍቅር ጤና እና ምቾትን እንድንላበስ ፈቃዱ ስለሆነ እነዚህን ሥራዎች በመስራት እና ትእዛዛቱን በፍቅር በመፈፀም ዳግመኛ ወደ ህይወት እሴቶች መምጣትን እርሱም ከእርሱም ቀጥሎ በእርሱ ትእዛዝ በሐዋሪያት እና በተከታዮቻቸው አማካኝነት አስረዳን። ህይወትንም ተስፋ አስደረገን።
ዓለምም ታሪኳ ተቀየረ፤ ሰው ዳግመኛ ደስታ እና የህይወት እሴቶች በሙላት በሚገኝበት መንገድ መጓዝ ጀመረ። የዓለም ስልጣኔ እና ውጤታማነት ቀያሿ ክርስቶስ ኢየሱስ ነው። የባርነት ህይወትን እና በሰው ነፍስ በመጫወት ደስታ እና ፈንጠዚያ የማይገኝ መሆኑን በማሳየት ለዓለም አልጫነቱን በማስወገድ።
 ይህንን ታሪካዊ ዳራ ለማንሳት ያስፈለገበት አሁን ያለንበት ዘመን ሰው የህይወት ስኬትን ከቁሳዊ ትርፎች ጋር በማያያዝ የተሳሳተ አቅጣጫን እየተከተለ ያለበት ዘመን በመሆኑ ነው። ይህ የአሁኑ የዓለም ሁኔታ ክርስቶስ በተወለደ ጊዜ እንደነበረው ሙሉ ለሙሉ የከፋ ባይሆንም በአብዛኛው የዓለም ክፍል ግን ሁኔታው ከዚያ ጊዜ ይልቅ እየከፋ መሆኑን መገንዘብ ይቻላል።   

 …ይቀጥላል…

Tuesday, July 5, 2011

የቤተክርቲያን የመከራ ዘመናት - ዛሬስ ሰላም ነውን? (ክፍል ስድስት)


በባለፈው ለመመልከት እንደሞከርነው ኢትዮጵያ ከዮዲት ጉዲት የጥፋት ዘመን በኋላ የአክሱም ሥርወ መንግስት እየተዳከመ ሄዶ በዛግዌ ሥርወ መንግስት ተተካ። ኢትዮጵያ በዛግዌ ሥርወ መንግስት የተወሰኑ የሀገሪቱ ሰሜናዊ ጫፎች ላይ ያላት ቁጥጥር አነስተኛ ስለነበር በአሁኗ ኤርትራ የቀይ ባህር አዋሳኞች እና በቀይ ባህር ውስጥ ባሉት ደሴቶች ላይ የነበሩ ጎሳዎች የእስልምና ሰለባ በመሆን በኋላም በኢትዮጵያ  መካከለኛው የታሪክ ዘመን ጥቃቅን የእስልምና ሱልጣኖች እንዲመሰረቱ ጥርጊያ መንገድ ከፈተ። የሰሜናዊ የባህር በሮችን በመጠቀምም በመሀል ሀገር ላይ ያሉት የተለያዩ ክፍሎች የራሱን አሉታዊ ተፅዕኖ ሊያሳርፍ እና የእስልምና እምነት እንዲስፋፋ የበኩሉን አስተዋፅኦ አድርጓል።
እነዚህንና የመሳሰሉትን ድክመቶች ቢያስተናግድም የዛግዌ ሥርወ መንግስት በዮዲት ጉዲት ዘመን በሀገሪቱ እና በቤተክርስቲያኗ ላይ ከደረሰው ጥፋት መልሶ ማንሰራራት ብሎም ሁነኛ የሚባሉ ድንቃድንቅ የአቢያተ ክርስቲያናት መታነፅ እና የቤተክርስቲያን ትምህርት መስፋፋት ትልቅ አስተዋፅኦ የከፈተ እና ኢየሩሳሌምን የሚተካ የአፍሪካ ኢየሩሳሌም (Jerusalem of Africa) እየተባለ የሚጠራውን የላልይበላ ውቅር አቢያተ ክርስቲያናት የተሰሩበት እና ቤተክርስቲያኗ በሀገሪቱ የነበረውን የሥነ-ፅሑፍ የሥነ-ሕንፃ እና አያሌ ኪነ-ጥበባዊ ሥራዎች የመራችበት እና አርአያ የሆኑ ቅዱሳን አባቶችን ንግስናን ከክህነት ጋር አስተባብረው የያዙ በጥበብ እና በመንፈስ ቅዱስ የተመሉ ሆነው ሕዝቡን በቀና መንገድ የመሩ ነገስታትን ለሀገሪቱ ያበረከተችበት ዘመን ነበር።
በሀገሪቱ ሰሜናዊ ጫፍ ያለው ክፍል ለእስልምና ተፅዕኖ ቢደርስበትም በደቡባዊ አቅጣጫ ክርስትና የተስፋፋበት ዘመንም ነበር። በዛግዌ ሥርወ መንግስት ጊዜ የነበረውን ሥራ በኢትዮጵያ ባይሠራ ኖሮ ዮዲት ጉዲትን ተከትሎ የሚመጣው የቤተክርስቲያኗ ዕድል ምን ይሆን እንደነበር መገመት አያዳግትም። የዮዲት ጉዲት ዘመን ከጥላቻ ያለፈ የራሱ ራዕይ እና ግብ ስላልነበረው ሀገሪቱ ወደ ይሁዲነት ባትቀየርም እንደ ዛግዌ ያለ የተደላደለ እና ጠንካራ ሥርወ መንግስት ባናገኝ ምናልባትም በዚህ በተዳከመ ጊዜ የመጣ ርህራሄ የለሽ የኦትማን ቱርክ ሰለባ እንሆንና ቤተክርስቲያኖቻችን በቁስጥንጢንያ (Constantinople) በዛሬዋ ቱርክ ውስጥ የሚገኘውን የቅድስት ሶፍያ ቤተክርስቲያን እጣ ይደርባቸው ነበር። ሀገሪቱም እንደቱርክ እና እንደ ግብፅ የክርስትና መናብርት እንዳልነበሩ ሁሉ ዛሬ እስላማዊ መንግስት ክርስትናን መድረሻ ያሳጡ እንደሆኑት ያለ ዕድል ይገጥማት ነበር። የዛግዌ ሥርወ መንግስት የኦትማን ቱርኮች ዓለምን ያሳድዱ እና ሀገራትን ይወሩ በነበረበት ዘመን ጠንካራ ሥርወ መንግስት ስለነበር ከዚያ ቀጥሎም በሰሎሞናዊ ሥርወ መንግስት ቢተካም ይህ ሰሎሞናዊ ሥርወ መንግስት ጠንካራ ስለነበር የኦትማን ቱርኮችም ሙሉ ሃይላቸው አውሮፓውያንን መውጋት እና የመስቀል ጦርነትን ድል ማግኘት ስለነበር ከትንኮሳ ያለፈ ነገር ባለማድረጋቸው እና ሀገር ውስጥ ያሉ ጥቃቅን ሱልጣኖችን በመርዳት በሀገሪቱ ላይ በቀላሉ ባለድል እንሆናለን ብለው ይገምቱም ስለነበር የእነዚህን ሱልጣኖች ትንኮሳ ተቋቁሞ በሀገሪቱ እና በቤተክርስቲያናችን ላይ የነበረውን አወንታዊ ዕድገት ሊገቱት አልቻሉም።
የዛግዌ ሥርወ መንግስት ከቅዱስ ላልይበላ መሞት ቀጥሎ በነበረው የሥልጣን ሽኩቻ  እየተዳከመ ሄዶ በሰሎሞናዊ ሥርወ መንግስት ሲተካ የመናገሻ ከተማ ከላስታ ወደ ሸዋ ዞረ። ይህ የመናገሻ ቦታ መዞር በሀገሪቱ ሰሜናዊ ጫፍ የነበረው ቅጥጥር በዚያው ልክ እየላላ በዛግዌ ሥርወ መንግስት የተፀነሱት ሱልጣኖች እየተጠናከሩ መጥተው መኖራችውን የሚያሳውቅ ተፅዕኖ እና ከኦትማን ቱርኮች በሚደረግላቸው ድጋፍ ማዕከላዊ የሀገሪቱ መንግስት ላይ ትንኮሳ ጀመሩ። የሰለሞናዊ ሥርወ መንግስት እንደ ዛግዌ ሥርወ መንግስት እጅግ ጠንካራ ባለመሆኑ በሀገሪቱ ማዕከላዊ እና ምስራቃዊ ቦታዎች በኢፋት እና በሀረር የተላዩ ሱልጣኖች በቅለው ማደግ ጀመሩ። በዚህም በሰሜንም በምስራቅም አቅጣጫ የሚመጡ የእነዚህን ሱልጣኖች ትንኮሳ መከላከል ለሥርወ መንግስቱ ሌላ የቤት ሥራ ሆኖ ነበር።
እነዚህን ተፅዕኖዎች በመቋቋም ይህ ሰሎሞናዊ ሥርወ መንግስት በዛግዌ ሥርወ መንግስት የተጀመረውን ሐይማኖታዊ እድገት ለ፫፻ ዓመታት ያህል ለማስቀጠል ችሏል። ይህ ከ፲ኛው እስከ ፲፭ኛው መ/ክ/ዘመን ያለው ጊዜ ወርቃማው የቤተክርስቲያን ጊዜ ይባላል። ቤተክርስቲያን በዮዲት ጉዲት ከደረሰባት ጥፋት አገግማ ለዛሬ ማንነታችን ትልቅ ድርሻ ያላቸው የቤተክርስቲያን ሥራዎች የፈለቁበት እና ክርስትናን በማስፋፋት እና የተለያዩ ታላላቅ አድባራት እና ገዳማትን በማቋቋም እና መፃሕፍትን በመፃፍ ጉልህ ድርሻ የነበራቸው ታላላቅ ቅዱሳን ያፈራችበት ዘመን ነበርና። እነ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ እነ አቡነ ተክለ ሃይማኖት እነ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በዚህ ዘመን ከቤተ ክርስቲያን ጉያ የፈሩ ከዋከብተ ቤተክርስቲያን ናቸው።
ነገር ግን በ፲፭ኛው መ/ክ/ዘመን የመስቀል ጦርነትን ባለድል የሆኑት የኦትማን ቱርኮች ትኩረታቸውን ወደ ቀይ ባህር ዙሪያ በነበሩት አካባቢዎች አድርገው ስለነበር በተለያዩ አቅጣጫዎች የነበሩትን ሱልጣኖች የጦር መሳሪያ እርዳታ በመስጠት ክርስቲያናዊ የሆነውን ማዕከላዊ የኢትዮጵያን ሰሎሞናዊ ሥርወ መንግስት ማዳከም እና በመጨረሻም የማጥፋት እና ሀገሪቱን በሃይል ለማስለም ምስራቅ አፍሪካም በእስልምና እንድትጥለቀለቅ በዚህም በቀይ ባህር ዙሪያ ወደ ሩቅ ምስራቅ እና ሕንድ የሚደረገውን የአውሮፓውያንና የመካከለኛው ምስራቅ የንግድ እንቅስቃሴ ለመቆጣጠር እንዲያመች አልመው በመነሳታቸው ከተለያዩ አቅጣጫዎች የነበሩት ሱልጣኖች በተለይም የሀረር ሱልጣን ከፍተኛ የሆነ ሃይል አሰባስቦ በተላዩ ጊዜያት ጥቃት መሰንዘር ጀመረ። ማዕከላዊ የሰሎሞናዊ ሥርወ መንግስትም የእነዚህን ሱልጣኖች ለመመከት ለተወሰኑ ክፍለ ዘመናት ሲከላለከል ከቆየ በኋላ በመጨረሻ እየተዳከመ በመሄዱ እና የሀረር ሱልጣን ከኦትማን ቱርኮች ባገኘው ዘመናዊ የጦር መሳሪያ እስከ አፍንጫው የታጠቀ ስለነበር ድል ፊቷን በማዞር ለግራኝ አህመድ ቀናችለት። በዚህም ክርስቲያናዊ የሰሎሞን ሥርወ መንግስት ከሸዋ እየሸሸ በተለያዩ የጦር አውድማዎች ከግራኝ አህመድ ጋር ጦርነት ቢያካሂድም ድል አልቀናው ስላለ የሥርወ መንግስቱ መናገሻ ወደ ጐንደር ተዛወረ። ግራኝ አህመድም አብዛኛውን የሀገሪቱ ክፍል በቁጥጥሩ ሥር አውሎ ሕዝቡን ሁሉ በሃይል በማስለም ካህናትንና ለመስለም ፈቃደኛ ያልሆኑትን ምዕመናን በመጨፍጨፍ አቢያተክርቲያናትን እና ንዋያተ ቅድሳትን እንዲሁም መፃሕፍትን በማቃጠል እጅግ ከፍተኛ ጥፋት እያደረሰ እስከ ጐንደር ደረሰ። ይህም የጥፋት ዘመን ለ፲፭ ዓመታት ቆየ። ጐንደር በተደረገው የአፄ ገላውዲዎስ እና አህመድ ግራኝ ጦርነት አህመድ ግራኝ በአንድ ፖርቱጋላዊ ወታደር ተመትቶ ስለሞተ ተከታዮቹ ወደ ሀረር ተመልሰው ፈለሱ እና አብዛኛው የሀገሪቱ ክፍሎች ተመልሰው በክርቲያናዊ መንግስት ቁጥጥር ሥር ዋሉ።
ይህ የአህመድ ግራኝ የጥፋት ዘመን ብዙ እልቂት እና ብዙ ጥፋቶች ያስከተለ ነበር። 

በሚቀጥለው ክፍል በአህመድ ግራኝ የደረሰውን ጥፋት እና ከዚያም ቀጥሎ የፖርቱጋል የሮማ "ቤተ ክርስቲያን" መልዕክተኞች በሀገራችን የደረሰውን ከፍተኛ የመከራ ዘመን እንቃኛለን


         …ይቀጥላል…       

Wednesday, June 29, 2011

የቤተክርቲያን የመከራ ዘመናት - ዛሬስ ሰላም ነውን? (ክፍል አምስት)

ክርስትና በኢትዮጵያ በ፬ኛው መ/ክ/ዘመን ጀምሮ በነበረው እጅግ ጠንካራ የወንጌል እና የክርስትና ትምህርት መስፋፋት ብዙ ሕዝብ ከንጉሳውያን ቤተሰብ ጀምሮ እየተጠመቀ የክርትና ሐይማኖት ተከታይ ሆነ። ቅዱስ ፍሬምናጦስ አባ ሰላማ የኢትዮጵያ ጳጳስ ሆኖ እስከተሾመበት እስከ አብርሃ ወአፅብሃ ዘመነ መንግስት ድረስ የወንጌል ዜናዋ በሀገራችን ቢነገርም ሕዝቡን ግን በማጥመቅ የመንፈስ ቅዱስ ልጆች እንዲሆኑ ማድረግ አልተቻለም ነበር። በመካከለኛው ምስራቅ እና በሮማ ቤተክርስቲያን ውስጥ ይኖሩ የነበሩት ርቱዐነ ሐይማኖት አባቶች በሮም ቤተክርስቲያን አማካኝነት በኬልቄዶን ጉባኤ የተጀመረው ኢ-ፍትሐዊ ድብደባ እና እንግልት በ፭ኛው መ/ክ/ዘመንም ሐይማኖታችንን አንክድም ምስክርነታችን አይታጠፍም ባሉት ቅዱሳን አባቶች ላይ ስለቀጠለ ዘጠኙ (ተሰዐቱ) ቅዱሳን የሮማ ቤተክርስቲያን ታስተዳድራቸው ከነበሩት ከተለያዩ የሮም ግዛት ተሰደው በእግዚአብሔር መሪነት ወደ ኢትዮጵያ መጡ።
እነዚህ ቅዱሳን ወደኢትዮያ ከመጡ በኋላ ግዕዝ ቋንቋን በሚገባ አጥንተው የተለያዩ ቅዱሳት መፃሕፍትን ወደ ግዕዝ በመተርጎም ወንጌልን ለሕዝቡ እንዲስፋፋ ወንጌል በማስተማር የተለያዩ ገዳማትን በመመስረት ሥርዐተ ምንኩስናን በማስተማር እና በማስፋፋት የቤተክርስቲያንን ትምህርት (ግብረ ዲቁና እና ምስጢረ ክህነትን) በማስተማር ወዘተ የቤተክርቲያኗ የመሪነት ሚና በመንፈስ ቅዱስ እና በተለያዩ አገራዊ ጉዳይ ከፍተኛ እመርታ እንዲያሳይ አድርገዋል። እነዚህ ቅዱሳን በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ባፈሯቸው ሊቃውንት አማካኝነት በአራቱም አቅጣጫ ትምህርተ ሐይማኖት በሚገባ ተጠናክሮ ቀጠለ። እንግዲህ በዚህ ጊዜ ሀገሪቱ በዓለም አቀፍ ደረጃ ሃያል የነበረችበት እና በስልጣኔ ከፍተኛ ደረጃ የደረሰችበት ጊዜም ነበር። በዚህ ጊዜ የተለያዩ ቅዱሳን አባቶች የወጡበት ሲሆን ታላቁን ሊቅ ቅዱስ ያሬድን ኢትዮያ የወለደችው በዚህ ጊዜ ነበር። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ከ፬ኛው መ/ክ/ዘመን እስከ ፰ኛው መ/ክ/ዘመን ድረስ ከፍተኛ እድገት ያስመዘገበችበት እና በሀገሪቱ ሁለንተናዊ እድገት ላይ አወንታዊ የመሪነት ሚናዋን የተጫወተችበት ወቅት ነበር ማለት ይቻላል። በሀገር ውስጥ ብቻ ሳይሆን ከሀገር ውጭም በየመን የናግራን ሰማእታትን በይሁዲዎች መጨፍጨፍ ያስቆመች ብርሃኗ ከሕዝቧ ተርፎ ለዓለም ያበራበት ወቅት ነበር ማለት ይቻላል።
በዚህ ሁኔታ እያለች ነው እንግዲህ በመካከለኛው ምስራቅ የተነሳው የእስልምና ማዕበል በሀገሪቱ ላይ አሉታዊ ተፅእኖውን እያሳረፈባት የመጣው። እስልምና በ፯ኛው መ/ክ/ዘመን በአረቢያ ምድር ተጠንስሶ በሀገሬው ሰዎች ከፍተኛ ተቃውሞ ሲገጥመው "ነብዩ" መሀመድ ተከታዮቹን ኢትዮጵያ ውስጥ በየዋህነቱ እና በእንግዳ ተቀባይነቱ የታወቀ ንጉስ አለ እና ወደዚያ ሽሹ በማለት ወደ ሀገራችን ሲልካቸው ሀገራችን በመልካም ሁኔታ ተቀብላ ክርስቲያናዊ በሆነ መንገድ አስተናገደቻቸው። ይህም በወንጌል ከተፃፉት ስድስቱ ቃላተ ወንጌል አንዱ እንግዳ ሆኜ ብመጣ ተቀብላችሁኛል የሚለውን መተግበሯ ነበር። ኢትዮጵያ ይህን በማድረጓ በቁራን ላይ አደራ ተቀባይ እና ባለውለታ ተደርጋ ትፃፍ እንጅ በወቅቱ ከነበረው የእስልምና አፍራሽ ስራዎች ልትድን አልቻለችም። በሰሜናዊ የሀገሪቱ ክፍል የነበረውን የንግድ እንቅስቃሴ እንዲገታ እና ቀስ በቀስ ሀገሪቱ እየተዳከመች እንድትሄድ በኋላም የእስልምና መሪዎች ሰለባ እንድትሆን የማዳከም እቅድ ተነድፎ በሙስሊም መሪዎች ተተገበረ። በዚህ የተነሳ ሰሜናዊ የሀገሪቱ ክፍል ለምነቱን ከማጣቱ በተጨማሪ የንግድ እንቅስቃሴው እክል ሲገጥመው የአክሱም ሥርወ መንግስት ቀስ በቀስ እየተዳከመ መጣ።
ከዚህ በሀገሪቱ ማዕከላዊ መንግስት መዳከም ተከትሎ በ፱ኛው መ/ክ/ዘመን ዮዲት የተባለች አይሁዳዊት ሴት (ከፈላሻ ዘር) በሀገራችን ላይ ከፍተኛ የጥፋት ዘመን አዋጅ አውጃ ብዙ ቤተክርስቲያናት አድባራት ገዳማት ቤተመዛግብት ንዋተቅድሳት መፃሕፍት እና አልባሳት ተቃጥለዋል። በብዙ ሺ የሚቆጠሩ ክርስቲያኖች ዲያቆናት ካህናት መምህራን መነኮሳት እና ገዳማውያን ተሰውተዋል። ለ፵ ዓመታት ባደረሰችው የጥፋት ዘመቻ ብዙ የቤተክርስቲያን መረጃዎች ጠፍተዋል። ይህ የዮዲት ጉዲት ዘመን በሀገራችን ታሪክ ተወዳዳሪ የሌለው ከፍተኛ ጥፋት ያስከተለ እና ለረጅም ዘመናት የቆየ የሰቀቀን እና በሀገራችን ከነበሩት የቤተክርስቲያን አሰቃቂ የመከራ ዘመናት የመጀመሪያው ነው። በዚህ አሰቃቂ የግፍ እና የመከራ ዘመን የአክሱም ሥርወ መንግስት እጅግ ተዳክሞ የቤተክርስቲያኗ ትምህርትም ለ፵ ዘመናት ተስተጓጉሎ ቆየ።
የዮዲት ጉዲት ዘመን በቅርሶች እና መፃሕፍት መውደም በክርቶያኖች መጨፍጨፍ እና በአቢያተ ክርስቲያናት መቃጠል ከፍተኛ የሞራል እና የሥነልቦና ውድቀት ቢያጋጥምም የሐይማኖታዊ ባህል መዛባት እና የረጅም ጊዜ ጠባሳ በሕዝቡና በክርትና ሐይማኖት ላይ አልተወም። ይህም በሚከተሉት ምክንያቶች ነው፦
፩. በዚያ ጊዜ የነበረው የሕዝቡ የሥነልቦና ጥንካሬ በዚያ ጊዜ የነበረው ሕዝብ እና መንግስትም ቢሆን ለዓለማዊ ኑሮ ዋጋው አነስተኛ እና ከሞት በኋላ ያለው ህይወት አማራጭ የሌለው በሌላ ዝባዝንኬ እና እራስን በመደለል ሊታለፍ እና ሊናቅ የማይችል መሆኑ ሕዝቡ በሚገባ የተረዳው ሀቅ ነበር። በዚህ የተነሳ ሐይማኖትን ከመተው እና ሐይማኖታዊ ያልሆነ ድርጊት እና ሥራን በወቅቱ በነበረችው ጨካኝ አረመኔያዊ ጭፍጨፋ ከመበገር ይልቅ ሞቶ የህይወት አክሊልን መቀበል የሚመርጥ ለፅድቅ የጨከነ ልብ ያለው ሕዝብ ነበር ማለት ይቻላል።
፪. የበኢትዮጵያ ይኖሩ የነበሩት አይሁዶች (ፈላሾች) ከክርቲያኖች ጋር የነበራቸው የባህል ውርርስ እና መመሳሰል፦ አይሁዶች ከክርቲያኖች ክርቲያኖች ደግሞ ከልደተ ክርስቶስ በፊት በነበራቸው ኦሪታዊ ሐይማኖታዊ ልምድ የተነሳ በነበረው የባህል መመሳሰል የዮዲት ጉዲት የጥፋት ዘመቻ የባህል አብዮት አልነበረውም።
፫. የዮዲት የጥፋት ዘመቻ በውል የታወቁ ግቦች ስላልነበሩት፦ ከክርትና ወደ ይሁዲነት በሃይል ለመቀየር ከመታሰቡ በቀር ከጭፍን ጥላቻ የመነጨ ስለነበር የራሱ ግብ ያለው ዘመቻ ስላልነበር ስር ነቀል የሐይማኖታዊ ባህል ለውጥን መሰረት ያደረገ አልነበረም።
፬. ከጥፋት ዘመኑ ማለፍ በኋላ የተከናወነው የመልሶ ማቋቋም ከፍተኛ ጥረት የተለያዩ ቅዱሳን በቃላቸው ያጠኑትን በብራና ላይ በመፃፍ እና በተለያየ ምክንያት ከጥፋት የተረፉትን ደግሞ በማባዛት አዳዲስ መፃሕፍትንም ፅፎ ለተላዩ በሐገሪቱ በሚገኙ ት/ቤቶች በማሰራጨት የተቃጠሉ አቢያተክርስቲያናትን መልሶ በማቋቋም እና በመገንባት ከፍተኛ ጥረት በመደረጉ በዚህ ዘመን የደረሰው የጥፋት ቁስል ወዲያውኑ ሊያገግም ችሏል። ይህም ወርቃማው የሥነፅሑፍ ዘመን ተብሎ የታወቀውን ብዙ አባቶቻችን እስከዛሬ የምንገለገልባቸውን መፃሕፍት የፃፉ እና ወንጌልን በድፍረት የጣኦት አምልኮ ያመልኩ ከነበሩ መሳፍንት እና የተለያዩ ጎሳዎች ድረስ የተሰበከበትን ዘመን አስከትሏል። ይህ ዘመን ቤተክርስቲያን ተመልሳ ያበበችበት ዘመን ነበር።
በእስልምና እና በዮዲት ጉዲት አሰቃቂ ዘመን አሉታዊ ተፅዕኖ ምክንያት የአክሱም ሥርወ መንግስት እየተዳከመ ሄዶ መጨረሻ የዛግዌ ሥርወ መንግስት ተመስርቶ የአክሱም ሥርወ መንግስት ሕልውና በዚሁ አከተመ። የዛግዌ ሥርወ መንግስትም የመናገሻ ከተማውን ከአክሱም ወደ ደቡብ አቅጣጫ ወደ ላስታ አዛወረው።
ኢትዮጵያ በዛግዌ ሥርወ መንግስት አስተዳደር ከሀገሪቱ ሰሜናዊ ጫፍ በአንፃራዊነት ወደ ደቡብ በመሸሿ ምክንያት ሰሜናዊ የኤርትራ ክፍለ ግዛቶች የእስልምና ተከታይ ነጋዴዎች መፈንጫ እንድትሆን በር የከፈተ ሲሆን በሀገሪቱ ላይ ያሉትን የንግድ ወሳኝ መስመሮችንና የባህር በሮችን ለመቆጣጠር አዳጋች ስለነበረ የሀገሪቱ ምጣኔ ሀብታዊ እድገትም የዚያኑ ያህል አዝጋሚ እንዲሆን ተገዷል። በባህር በር አካባቢ ያሉ የሀገሪቱ ጎሳዎች የእስልምና ሰለባ መሆን እስልምና ወደ ሀገሪቱ በወላሉ የመግቢያ እና የመቦረቂያ በር ክፍት ሆኖ የራሱን አሉታዊ ተፅዕኖ በቤተክርስቲያን እድገት ላይ አሳርፏል። በርግጥ የሀገራችን ልዕልና ከአክሱም ሥርወ መንግስት ጊዜው ጋር ሲመዛዘን ያነሰ ቢሆንም ሀገሪቱ በዛግዌ ሥርወ መንግስትም የሀገራችን የሞራል ልዕልና እና የኪነጥበብ እድገት ከፍተኛ ደረጃ የደረሰበት እና ሐይማኖታዊ እድገትም እንደተመዘገበ በዘመኑ ከተሰሩ ሥራዎች ምስክርነት እና ከተለያዩ የታሪክ ድርሳናት መገንዘብ ይቻላል።
በሚቀጥለው ክፍል ደግሞ በዛግዌ ሥርወ መንግስት የነበረው የሐይማኖታዊ እድገት ተመልሶ ማበብ እና የመካከለኛው ዘመን የሀገሪቱን ታሪክ እንቃኛለን።
...ይቀጥላል…



Thursday, June 23, 2011

የቤተክርቲያን የመከራ ዘመናት - ዛሬስ ሰላም ነውን? (ክፍል አራት)

ከዛሬ ጀምሮ ደግሞ ስለ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ተከታታይ ፅሑፎችን ለመመልከት እንሞክራለን።
የኢትዮጵያን የክርስትና አመጣጥ እና አምልኮተ እግዚአብሔር ስንመለከት ታሪኩ ከክርስቶስ ልደት በፊት ብዙ ሺ ዘመናትን አቋርጦ ወደ ኋላ ይወስደናል ይህም ኢትዮጵያ በሦስቱም ዘመናት እግዚአብሔርን እያመለከች የምትኖር ብቸኛ ሀገር ያደርጋታል። ውም በዘመነ ሕገ-ልቦና በዘመነ ኦሪት እና በዘመነ ወንጌል ናቸው። የኢትዮጵያን በዘመነ ሕገ-ልቦና እግዚአብሔርን ታመልክ እንደነበር የሚያሳየው በዘፀአት ላይ የተፃፈው የሙሴ ወደ ምድያም ምድር መሰደድ እና በዚያም የካህኑ የዮቶር በጐች ጠባቂ እንደነበር የካህኑ የዮቶርን ልጅም አግብቶ እንደነበር በዚህም በኋለኛው ዘመን እስራኤልን ከግብፅ ባርነት አውጥቶ እየመራ ወደ ከነአን ምድር ሲወስዳቸው ኢትዮጵያዊቱን በማግባቱ በእህቱ በማሪያም እና በወንድሙ በአሮን ተቃውሞ እንደገጠመው ያሳያል። ዮቶር ካህን መሆኑ የሚያስረዳው በኢትዮጵያ ከሙሴ ወደ ካህኑ ዮቶር መምጣት በፊት በውል የተረዳ እና ለብዙ ጊዜ የቆዬ አምልኮተ እግዚአብሔር እንደነበር ነው። ከዚህም በተጨማሪ ካህኑ እና የሳሌም ንጉስ መልከጼዴቅ ኢትዮጵያዊ መሆኑ እና ኢየሩሳሌምንም መመስረቱ በኢትዮጵያ ለረጅም ዘመን ፀንቶ የቆየ አምልኮተ እግዚአብሔር እንደነበር ያሳያል።
በመፅሐፍ ቅዱስ በተለያዩ ክፍሎች እንደተገለጠው ኢትዮጵያ የሚለው ስያሜ እንኳን የተወሰደው ኩሽ የተባለ የኖህ የልጅ ልጅ (የካም ልጅ) የመሰረታት ሀገር መሆኗን እና በስሙም ኩኝ ተብላ የምትጠራ ሀገር እንደነበረች ኢትዮያ የሚለው ስያሜም ብሉያት መፅሐፍትን ከእብራይስጥ ወደ ፅርዕ ቋንቋ የተረጎሙ ሰብአው ሊቃናት ኩሽ የሚለውን በተለያዩ የብሉያት መፅሓፍት ያለውን የሀገሪቱ ስም ኢትዮያ ብለው እንደተረጎሙት ይህም የኩሽ ሌላው ስሙ ከሆነው ኢትዮስ የተወሰደ መሆኑን እንገነዘባለን።
ኦሪት ሕግ በሲና ምድረ በዳ በሙሴ በኩል ከተሰጠ ከ፪፻ እስከ ፫፻ ዓመታት ጊዜ በኋላም ንጉስ ሰሎሞን የእስራኤል ንጉሳቸው በነበረበት እና በኢትዮያም ንግስት ማክዳ በነገሰችበት ዘመን የሰሎሞንን ጥበብ ለማየት ወደ ኢየሩሳሌም የኢትዮያ ንግስት በተጓዘችበት ጊዜ ከንጉስ ሰሎሞን ፀንሳ ስለተመለሰች ቀዳማዊ ሚኒሊክን ወለደች። ቀዳማዊ ንጉስ ሚኒሊክም ፳፪ ዓመት በሞላው ጊዜ ወደ ኢየሩሳሌም ተመልሶ ሄዶ ከአባቱ ዘንድ ለ፫ ዓመት ያህል ሥርዓተ ንግስናን ተምሮ ሕገ ኦሪትን እና ከሙሴ እስከ ሰሎሞን ያሉትን የብሉያት መፃሕፍት ይዞ ፫፻፲፰ ሌዋውያን ካህናትንና ወደ ፲፪ ሺ የእስራኤል የበኩር ልጆችን አስከትሎ ወደ ኢትዮያ መጣ።
በዚህ ጊዜ ነው እንግዲህ ሀገራችን ኢትዮያ ከሕገ-ለቦና ወደ ዘመነ ኦሪት የተሸጋገረችው። በመፅሐፍ ቅዱስ ላይ ካሉት የተለያዩ ማስረጃዎች በተጨማሪ ሀገራችን በዘመነ ኦሪት አምልኮተ እግዚአብሔር ስትፈፅም የነበረች መሆኗን እስከ አሁን ህያው በሆኑት የኦሪት መስዋዕት ሲሰዋባቸው የነበሩ የተለያዩ አድባራት እና ገዳማት እንዲሁም በውስጣቸው የሚገኙት ንዋተ ቅድሳት ቋሚ ማስረጃዎች መረዳት ይቻላል። ከዚህ መተጨማሪ የሕዝቡ አኗኗር እና ሐይማኖታዊ ባህሉ የኦሪት ዘመን ትላልቅ አሻራዎች ናቸው።
ኢትዮያ ከእስራኤል ጋር በነበራት ጥብቅ ግንኙነት ከሰሎሞን በኋላ የተፃፉትን የነቢያት መፃሕፍት በየጊዜው ተከታትላ በማስገባትና ሁሉም መፃሕፍት ወደ ግዕዝ ቋንቋ ተተርጉመው ሕዝቡ እንዲገለገልባቸው ስታደርግ እና እግዚአብሔር ጋር የነበራትን ጥብቅ ግንኙነት አጠናክራ ለመቀጠል ችላለች። እንዲያውም በአንድ ወቅት ናቡከደነፆር እስራኤልን በማረከ እና ኢየሩሳሌምን ባቃጠላት ጊዜ በእስራኤል የነበሩት ከዚህ ዘመን በፊት የጠፉ የብሉያት መፃሕፍት ምንጭ በመሆን የቅዱሳት መፃሕፍትን መጥፋት ታድጋለች።
ኢትዮያ በነቢያት የተነገረውን እና በብሉያት መፃሕፍት የተፃፈውን የመሲህ ክርስቶስ መምጣት ነቅታ እና ተግታ ተስፋዋን እየተጠባበቀች ሳለ ከብዙ ዘመን በፊት በነበረ የኢትዮያ ንጉስ አማካኝነት በእግዚአብሔር ገላጭነት ቅድስት ድንግል ማሪያም ከተወደደው ልጇ ጋር ሆኖ የተሰራ ስዕለ አድህኖ ያለበት የኮከብ ቅርፅ ሰርቶ ዓለምን ሊያድን የሚመጣው የእግዚአብሔር ልጅ ከዚህች ቅድስት ንፅህት ድንግል በሥጋ እነደሚወለድ ለልጆቹ ነግሯቸው። ይህ ትንቢት ሲፈፀም ይህ ኮከብ ካለበት ተነስቶ ብርሃን እያበራ መሲሁ ከተወለደበት ቦታ እንደሚሄድ እና ይህ ክስተት ሲከሰት ተከትለው ሄደው እንዲሰግዱለት እና ግብርም እንዲገብሩለት አደራ ትቶላቸው እንደሞተ እና ይህ አደራ ከልጅ ልጅ እየተላለፈ ጌታችና መድኒታችን በቤተልሔም ከእመቤታችን ሲወለድ የነበረው የኢትዮያ ንጉስ ባዜን የተተወለትን አደራ ተቀብሎ ወርቅ እጣን እና ከርቤ ይዞ ኮከቡን ተከትሎ ወደ ቤተልሔም እንደሄደ በመንገድም ሌሎች የፋርስ እና የባቢሎን ነገስታት አብረውት እንደሄዱ ወንጌልም ሰብአ ሰገል (የጥበብ ሰዎች) ብሎ ከሚጠራቸው አንዱ የኢትዮያ ንጉስ እንድሆነ ይነገራል።
እንዲሁም በሐዋሪያት ሥራ ላይ እንደተገለጠው የኢትዮያ ንግስት ህንደኬ ጃንደረባ ወደ ኢየሩሳሌም ሊሰግድ እና ሊሳለም እንደሄደ በዚያም በጌታችን ፈቃድ እና በሐዋሪያው በፊሊስ አስተማሪነት እና አጥማቂነት የወንጌል ዜናዋ ወደ ኢትዮያ ጌታችና እና መድኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአረገ በአስረኛው ቀን እንደተሰበከ እንረዳለን ይህም የቤተክርስቲያን ልደት ተብሎ በሚጠራው እና በሐዋሪያት ላይ መንፈስ ቅዱስ በወረደበት ቀን የኢትዮያ ቤተክርስቲያንም በዚያችው እለት በኢየሩሳሌም በነበረው ጃንደረባዋ ልደቷ ሆነ። ጌታችና መድኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋሪያትን “እናንተስ እኔ ማን እንደሆንኩ ታላላችሁ?” ብሎ በጠየቃቸው ሰዓት ቅዱስ ጥሮስ “አንተ የሕያው የእግዚአብሔር ልጅ ነህ” ብሎ የመሰከረውን ቃል ይህ የኢትዮያ ጃንደረባም ፊልስን “እንዳልጠመቅ ምን ይከለክለኛል?” ብሎ ሲጠይቀው “ብታምን ተፈቅዷል” ባለው ጊዜ “ኢየሱስ ክርቶስ የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን አምናለሁ” በማለት የቅዱስ ጥሮስ መልስ እና እምነት የቤተክርስቲያን መሰረት የሆነ ዐለት እንደሆነ ሁሉ የቅዱስ ጥሮስን እምነት ይህ ጃንደረባ ይዞ በመገኘቱ ለኢትዮያ ቤተክርስቲያን የማይነቃነቅ መሰረት ሆኖ በዚች ቀን የኢትዮያ ቤተክርስቲያንም ተወለደች።
ከቤተ አይሁድ ተለይታ ክርስቶስን በመቀበል እና ከሌሎች በዓለም ላይ ከሚገኙት አቢያተ ክርትያናት ተለይታ ከአምልኮት እግዚአብሔር ወደ አዳም ተስፋ ፍፃሜ ወደ ሆነው ክርስትና ተሸጋገረች። ይህ የወንጌል ዜና በዚህ ጃንደረባ አማካይነት መጀመሪያ ከቤተመንግስቱ ሰዎች ጀምሮ እስከ ተራው ሕዝብ የተዳረሰ ሲሆን በኢትዮያ ወንጌል ተስፋፍቶ መፃሕፍት በስፋት እየተተረጎሙ ትምህርት በስፋት መሰጠት የተጀመረበት እና ሕዝቡ ከመንፈስ ቅዱስ ዳግመኛ እንዲወለድ ማጥመቅ የተጀመረው በ፬ኛው መ/ክ/ዘመን ሶሪያዊው ቅዱስ ፍሬምናጦስ በቅዱስ አትናቲዎስ እጅ ጵጵስና ተሹሞ ወደ ኢትዮያ በተመለሰ ጊዜ ነበር። ከዚህ ዘመን ጀምሮ ደግሞ የሐዲሳት መፃሕፍት ከተለያዩ ቋንቋዎች ወደ ግዕዝ እየተተረጎሙ በስፋት ትምህርት ለሕዝቡ ሁሉ መሰጠት የተጀመረበት እና ክርስትና ተጠናክሮ የተጀመረበት ነበር።
በሚቀጥለው ክፍል ደግሞ ከዘጠኙ ቅዱሳን ወደ ኢትዮያ መምጣት በኋላ በኢትዮያ የነበረውን ሁኔታ እንመለከታለን።
…ይቀጥላል…

Saturday, June 18, 2011

የቤተክርቲያን የመከራ ዘመናት - ዛሬስ ሰላም ነውን? (ክፍል ሦስት)

የሮማ ቤተክርስቲያን ውስጣዊ የሐይማኖታዊ የባህል እና የአመለካከት ልዩነትን በውስጧ ከ፮፻ ዓመታት በላይ ስታስተናግድ ኖራ በመጠጨረሻ በላቲን ቋንቋ ተናጋሪ በሆነው የሮማ ምዕራባዊ ቤተክርስቲያን ፓፓ እና የፅርእ ቋንቋ ተናጋሪ የነበረው የምስራቅ የሮማ ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪ በነበረው ፓትሪያርክ እና አንዳንድ የቤተክህነት አለመግባባት እርስ በእርስ ተወጋግዘው ተለያዩ። ሁለቱ ቤተክርስቲያናት ከኦሬንታል ቤተክርስቲያን በብዙ የሚለያዩ ሲሆን እርስ በእርሳቸው ግን ተቀራራቢነት ያላቸው ናቸው።
በአስራስድስተኛው መ/ክ/ዘመን በሮማ ቤተክርስቲያን በነበረው ብልሹ አሰራር እና ስጋዊ አስተሳሰብ ምክንያት ምእመናኑ እና አንዳንድ የመሪነት ደረጃ የተነፈጋቸው ካህናት እና መነኮሳት ባስነሱት ማጉረምረም ሊከሰሰስ እና ሊወቀስ የማይችል ፍፁም ነው ተብሎ በሚታመነው የቤተክርስቲያኒቱ መሪ ፓፓ ላይ ከፍተኛ ተቃውሞ ይዞ እንዲነሳ ሉተርን አደፋፈረው።
በእርግጥ ሉተር ባለፈው ክፍል ለመግለጥ እንደተሞከረው እግዚአብሔር በሰጠው አእምሮው ተመራምሮ የሮማ ቤተክርስቲያን በመንፈስ ቅዱስ ሳይሆን በስጋዊ ሀሳብ እና በፓፓዎቹ ምኞት እና ፈቃድ የምትተዳደር እና መንፈስ ቅዱስ የራቃት መሆኗን ሳይገነዘብ አልቀረም። ነገር ግን ሌላ እርሱ የረሳው ነገር ግን አለ።
ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቂሳሪያ በነበረ ጊዜ ሐዋሪያትን ስለራሱ በጠየቃቸው ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ ‘ አንተ የህያው የእግዚአብሔር ልጅ ነህ” በሎ ሲመልስ ጌታችን የተናገረውን እረስቶታል። ይህም ‘የዮና ልጅ ስምዖን! አንተ ብፁዕ ነህ በሰማይ ያለው አባቴ ነው እንጅ ስጋዊ ደማዊ አልገለጠልህም። አንተ መሰረት እንደሆንክ እኔ እነግርሃለሁ፤ በዚያች መሰረት ላይም ቤተክርስቲያኔን እሰራታለሁ፤ የሲኦል በሮችም አይበረቱባትም።” ማቴ. ፲፮ ፥፲፰
ወደሌላ አማራጭ ከመግባቱ በፊት የቤተክርስቲያን እውነት ለዘመናት ሳይቋረጥ እንደ ጅረት ሲፈስ እና ምእመናኑን ሁሉ ሲያጠጣ የሚኖርባት የሲኦል በሮች የማይበረቱባት እውነተኛዋ ሐይማኖት የሮማ ቤተክርስቲያን አለመሆኗን ካረጋገጠ ያች የሲኦል ደጆች ሊያጠፏት የማይቻላቸው ቤተክርስቲያን የት አለች? ብሎ መጠየቅ ነበረበት።እርሷም በወቅቱ በእስክንድሪያ መንበረ ማርቆስ የምትመራው የመጀመሪያው የሐዋሪያት ስብከት ህያው የሆነ ዶግማ እና ቀኖና እንዲሁም ሐይማኖታዊ ባህል ይዛ ለትውልድ ለማስተላለፍ አደራዋን የተወጣች የኦሬንታል ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን ናት።
ሉተር ይህንን ነገር ምንም ሊያስበውም የማይፈልግ ነበር። ይህም ምክንያቱ የተለያየ ሲሆን በመጀመሪያ ደረጃ እርሱም በመንፈስ ቅዱስ የሚመራ ሳይሆን ሳይገባው ገዳማዊ ህይወትን ጀምሮ የምንኩስና ህይወትን የጠላ እና ለስጋዊ ተግባራት ያጋደለ አቋም ስለነበረው ከሞት ክልል እራሱን ነፃ አውጥቶ እንደ አብርሃም እውነትን ፍለጋ እንኳን እስከ መንበረ ፀባኦት ይቅርና ከሰዎች ጠይቆ ለመረዳት እስከ እስክንድሪያ መንበረ ማርቆስ እንኳን ለመገስገስ የሚያግዝ መንፈሳዊ ብርታት አልነበረውም። ስለዚህ በወቅቱ የአውሮፓ መንግስታት በመስቀል ጦርነት ምክንያት ከገቡበት ከፍተኛ ቀውስ ገና ባለማገገማቸው እና ሕዝቡ ሁሉ በዚህ ከፍተኛ የሞራል ኪሳራ በነበረበት ወቅት ውስጥ ስለነበረ የተገኘውን አማራጭ ከመከተል ወደኋላ የማይል እና በሮማ ቤተክርስቲያን ያለአግባብ ብዝበዛ የተሰላቸበት ዘመን ስለነበረ ሉተር ደፍሮ ጣቶቹን በፓፓው እና በከፍተኛ የቤተ ክህነት ሰዎች ላይ ባለ ፺፱ የተቀውሞ ነጥቦችን አንግቦ በመነሳቱ ብዙ ተከታይ በአጭር ጊዜ ሊያፈራ ችሏል
ይህ የሉተር ፍልስፍና መላዋ አውሮፓን አጥለቀለቃት። የተለያዩ የሐይማኖት ዶግማና ቀኖና ያላቸው የፈቃዳቸውን መፈፀም የሚችሉበት አዳዲስ ቤተእምነቶች በለመላው አውሮፓ እንደ አሸን ፈላ። ዛሬ ዛሬ በተለያዩ የዜና ምንጮች እንደምንረዳው ይህ የሉተር የሞት መንገድ በመፅሐፍ ቅዱስ ተለይቶ የተቀመጠን አንድ ሀገር በዲን እሳት እስከመጥፋት ያደረሰ ሐጢያት ሳይቀር ‘በደል ሆይ ወዴት አለሽ?” እያሉ በአሰሳ በመፈለግ የቤተእምነታቸው ስርዓት በማድረግ ላይ ናቸው። የሞት መንገድ መሆኑን እንኳን ሐይማኖተኛ ሰው ይቅርና ማንም ሰው እንከተለዋለን እንረዳዋለን በለው በሚያመካኙት መፅሐፍ ቅዱስ አማካኝነት ከንቱነታቸውን ጠንቅቆ ያውቃል። የእነ ሉተር ጅምር በዚህ ብቻ አላበቃም። ብዙ ሰይጣኒዝም (ሰይጣንን ማምለክ) የጀመሩ አቢያተ እምነት መነሻቸው ሉተራዊ አስተሳሰብ እና ከሉተር ልጆች አስተሳሰብ የመነጨ መሆኑ የአደባባይ ምስጢር ሆኗል።
በአሁኑ ጊዜ በዓለም ላይ አስር ሺ በላይ የሚሆኑ አቢያተ እምነቶች ያሉ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ ከሁለት ሺ ሁለት መቶ በላይ የሚሆኑት የክርስትና እምነት እና በመፅሐፍ ቅዱስ ላይ የምንመራ ነን ይላሉ። እነዚህም ድርጅቶች የወጡት ከሉተራዊ አስተሳሰብ ሲሆን ይህ የሮማ ቤተክርስቲያን እና ሉተራዊ ቤተእምነት በመንፈስ ቅዱስ የሚመሩ ባለመሆናቸው እነዚህን ሁሉ ቤተእምነቶች ወለዱ። ነገር ግን ብዙ ሐይማኖት እንደሌለ በመፅሐፍ ቅዱስ በቅዱስ ጳውሎስ መልእክት ወደ ኤፌሶን ሰዎች ፬፥፬ - ፮ ላይም እንደተገለፀው አንድ ጌታ አንዲት ሐይማኖት እና አንዲት ጥምቀት ብቻ እንዳለ እንረዳለን። ይህችም በመንፈስ ቅዱስ መሪነት የጌታችን እና የመድኃኒታች የኢየሱስ ክርስቶስን ትምህርት እና እርሱም የባህርይ አምላክ እመቤታችን ድንግል ማሪያምም ወላዲተ አምላክ እንድሆነች ሐዋሪያት ከጌታችን ተቀብለው የሰበኩትን እና ያስተማሩትን ዶግማውን ቀኖናውን እና ህይወቱንም ጭምር ለዘመናት አሻግራ ለትውልድ ያቆየች ብቸኛዋ የኦሬንታል ቤተክርስቲያን እንደሆነች እናምናለን፤ ከብዙ ታሪካዊ እና ሌሎች የሰው አእምሮ መርምሮ ሊደርስበት የሚችለውን እኛው መርምረን እና ከሰው ህሊና በላይ የሆነውን ደግሞ በመንፈስ ቅዱስ ገላጭነት በቅዱሳን አባቶቻችን በኩል ተረድተን መንገዳችን ከሰማያዊት ኢየሩሳሌም የምታስገባ የጠበበችው መንገድ እንደሆነች እናውቃለን።
ከዚህ በፊት በነበሩን ሦስት ተከታታይ ፅሑፎች የቤተክርስቲያንን ታሪክ እና ውጣ ውረድ በዓለም አቀፍ ደረጃ በአጭሩ ተመልክተናል።
በሚቀጥሉት ተከታታይ ክፍሎች ደግሞ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ያሳለፈቻቸውን የፈተና ዘመናት እና አሁን ያለችበትን ነባራዊ ሁኔታ እንቃኛለን።
…ይቀጥላል…

Saturday, June 11, 2011

የቤተክርቲያን የመከራ ዘመናት - ዛሬስ ሰላም ነውን? (ክፍል ሁለት)

በእናት ቤተክርስቲያን ከ፷ ዓ.ም እንከ ፫፻፲፪ ዓ.ም ድረስ እጅግ አስከፊ እልቂት እና የስደት ዘመን የነበረ እና እጅግ ብዙ የቤተክርስቲያን ቅርሶች የወደሙበት ቢሆንም በዚህ ዘመን የነበሩት የክርስቲያኖች ሕብረት እጅግ የሚያስቀና አንዱ ሌላውን ለማዳን እራሱን አሳልፎ በመስጠት መድኃኒታችን ክርስቶስን የመሰሉበት የፍቅር ዘመን ነበር ማለት ይቻላል። ምንም እንኳ በዚህ ዘመን የነበሩት ክርስቲያኖች በቁጥር አናሳ ቢሆንም ፍሬው ግን ገለባ የሌለበት ንፁሕ እና ሚዛን የሚመታ የክርስትና ሕይወት የታየበት ዘመን ነበር ማለት ይቻላል። በዚህ ዘመን ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‘ሊከተለኝ የሚወድ መስቀሌን ተሸክሞ ይከተለኝ ‘ ብሎ ያዘዘንን ትእዛዝ በተግባር በማሳየት የተለያዩ ሰዎችን ወደ ሕይወት ጎዳና መመለስ ከሚቻልበት ሁኔታ በቀር በመድረክ እና በአደደባባይ ሰላማዊ ስብከት እና ትምህርት መስጠት እጅጉን አሰቸጋሪ የነበረበት ዘመን ነበር።
ይህ ዘመን አልፎ ቤተክርቲያን አንጻራዊ ሰላም ባገኘችበት ዘመን መልኩን ለውጦ የመጣው የዲያብሎስ ውጊያ አርዮሳውያንን አስነስቶ ምናልባትም በዐላውያን መንግስታት ከነበረው የበለጠ በቤተክርስቲያን ላይ ጉዳት አድርሶባታል። የአርዮሳውያን ተንኮል መልኩን እየቀያየረ ቆይቶ ንስጥሮስ ባስነሳው የኑፋቄ ትምህርት ላይ አባቶቻችን በኤፌሶን ተሰብስበው ያወገዙት ቢሆንም ይህንን መሰረት ያደረገ ሌላ የኑፋቄ ትምህርት ለማራመድ የቄልቄዶን ጉባኤ ላይ እራሳቸው ጉባኤ ጠርተው ፍትህ የጠፋበት ርትዕ ሐይማኖት ጠበቃ የነበሩ አባቶቻችን ጥርሳቸው እስኪረግፍ ጺማቸው እስኪነጭ የግፍ ግፍ ተደርጎባቸው የሮማን ንጉሳዊ ቤተሰብ ፍላጎት ያንፀባረቀው እና ይህንን የሮማን ወታደራዊ ኃይል መከታ ያደረገው በሮማ ጳጳስ ሊዮን ትእዛዝ ተደብድበዋል፤ በኋላም ግዞት ቤት ተለይተው እንዲታሰሩ ተደርገው በዚያው በእስር ላይ እንዳሉ አርፈዋል።
በዚህ ጊዜ (፬፻፶፩ ዓ.ም) ነው እንግዲህ ቤተክርስቲያን ለሁለት የተከፈለችው። በሰላሙ ጊዜ የተነሳው የውስጥ ጠላት ቤተክርስቲያንን ለሁለት ከፍሎ የጥፋት ልጆችን መለመለ። በእስክንድሪያ መንበረ ፓትሪያርክ ስር የነበሩት ኦርቶዶክሳዊት እና ርቱዕ የሆነች ሐይማኖትን ፍፁም ተዋህዶን ስትሰብክ የምዕራቡ እና በሮማ መንበረ ፓትሪያርክ በሊዮን ሥር እራሷን ዓለማቀፋዊት ነኝ ለማለት ‘ካቶሊክ” ብላ እራሷን ሰይማ ሁለት ባህርይን መስበክ ጀመረች። ከእግዚአብሔር ይልቅ ለሰዎች ክብር ከፍተኛ ጥንቃቄ ያደረገ እና ሥጋዊ ፍላጎታቸው ጐልቶ የታየበት ሥርዓትም አረቀቁ።
በዚህ ሁኔታ የሮማ ቤተክርስቲያን ሰባት ዓለማቀፋዊ የቤተክርስቲያን ጉባኤዎች አሉኝ፤ የእምነት መሰረቴ እነዚህን መሰረት ያደረገ ነው ትላለች። ከእነዚህም መካከል ሦስቱ ቤተክርሰቲያን ከመከፈሏ በፊት አርዮስን፣ መቅዶንዮስን እና ንስጥሮስን ለማውገዝ የተደረጉትንም ይጨምራል። እነዚህ ሦስት ጉባኤዎች ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን የምትቀበላቸው ብቸኛ ዓለማቀፋዊ ጉባኤዎች ሲሆኑ ከዚያ በኋላ የሮማ ቤተክርስቲያን አራት ዓለማቀፋዊ ጉባኤያት (የውሾች ጉባኤ እየተባለ የሚጠራው የኬልቄዶን ጉባኤን ጨምሮ) አከናውናለች። ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን ከእነዚህ ጉባኤዎች መካከል ተሳትፎ የነበራት በጉባኤ ኬልቄዶን ብቻ ቢሆንም በዚህ ጉባኤ የመንፈስ ቅዱስ መሪነት ቸል ተብሎ የሰዎች የግል ፍላጎት የተነፀባረቀበት እና ፍትህ የተጓደለበት የነገስታቱ ኃይል ተፅእኖ የፈጠረበት የሮማ መንበር የበላይነትን በመንፈስ ቅዱስ ፍቃድ ሳይሆን በንጉሳዊ ቤተሰቦች እና በሮማ የካህናት ቢሮክራሲ ፍላጎት ከእስክንድሪያ መንበረ ማርቆስ ለመንጠቅ የተሞከረበት የሰው አካል እስኪጎድል ድብደባ እና እንግልት የተፈፀመበት በመሆኑ በዚህ ጉባኤ የተከናወኑ ክንውኖችንም ሆነ ውሳኔዎች አትቀበላቸውም። ሌሎቹ ሦስቱ ግን በሮማ በብቸኝነት የተከናወኑ በመሆናቸው ሙሉ በሙሉ የሮም ቤተካህናት እና ንጉሳውያን የፈለጉትን የደነገጉበት በመሆኑ አትቀበለውም።
የሮማ ቤተክርስቲያን የሦስቱን የመጀመሪያ ዓለማቀፋዊ ጉባኤዎች እጋራለሁ ውሳኔዎቹምንም እቀበላለሁ ብትልም ውሳኔዎችን ግን ሽራቸዋለች። በኒቂያ ጉባኤ ሠለስቱ ምእት የወሰኑትን ሐይማኖት የሚጻረር ሐይማኖት ደንግጋቸች። ምንታዌነትን ስርዋፅ አስገብታ የአባቶች ውሳኔ ነው ትላለች። በዚህም ማንም ቀና አእምሮ ያለው ሰው ከ”ሐይማኖቶች” መካከል ትክክለኛውን ምረጥ ቢባል ታሪካዊ አመጣጣቸውን በሚገባ መርምሮ ወጥነት የሌለው እና ከጊዜ ወደ ጊዜ የሚዋዥቅ ሐይማኖት”ን በመንፈስ ቅዱስ መሪነት የሚመራ ቀጥተኛ ሐይማኖት አለመሆኑን ጠንቅቆ ይረዳል። ለታረካዊ የቤተክርቲያን የመጀመሪያ የመከፋፈል አደጋን እንዴት እንደነበር በአጭሩ እንዲህ ከተረዳን የሁለቱን ልዩነት በሚገባ ለማሳየት ግን ጊዜ ስለሚያንስ እግዚአብሔር ከፈቀደ በሌላ ጊዜ እንመለስበታለን።
በዚህ አኳኋን ቤተክርስቲያን ለሁለት ከተከፋፈለችበት ጊዜ ጀምሮ ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያናችን ህያው የሆነውን የሐዋሪያት ስብከትን መሰረት ያደረገ እና ሐዋሪያት የሰበሰቧትን ቤተክርስቲያንን ምንም ዝንፍ ሳያደርጉ ጠብቀው በትምህርታቸው በህይወታቸው በተጋድሏቸው እና መፃሕፍትን በመፃፍ እና የተለያዩ የቤተክርስቲያን ሥርዐቶችን በመንፈስ ቅዱስ መሪነት በመሥራት ለትውልደ ትውልድ ሳይቋረጥ ለዘመናት እንደሚፈስ ንፁሕ ወንዝ ከኛ ዘመን አደረሷት።
ይህችን ቀጥተኛ ሐይማኖት ይዘው የሚገኙ አምስቱ የምስራቅ አብያተ ክርስቲያናት (Oriental Orthodox Churches) የሚባሉት ኢትዮጵያ፣ ግብፅ፣ አርመን፣ ሶሪያ እና ህንድ ናቸው። ነገር ግን ሌሎች የምስራቅ (Eastern Orthodox Churches) የሚባሉም አሉ። እነዚህ አብያተ ክርስቲያናት ዶግማና ቀኖና የኛዎቹ (Oriental Orthodox Churches) ቤተክርስቲያናት ከሚከተሉት ዶግማና ቀኖና ይለያል። እነዚህ የምስራቅ (Eastern Orthodox Churches) የሚባሉት ከ፬፻፶፩ ዓ.ም እስከ ፲፻፶፬ ዓ.ም ድረስ በሮማ ቤተክርስቲያን ስር የቆዩ ሲሆኑ በ፲፻፶፬ ዓ.ም ከሮማ ቤተክርስቲያን ተገንጥለው የወጡ ነገር ግን በብዙ የዶግማ እና ቀኖና ይዘታቸው ከሮማ ቤተክርስቲያን ጋር አንድ የሆኑ በጥቂቱ ልዩነት ያላቸው የአንድ ሳንቲም ሁለት ገፅታዎች ናቸው።
በዚህ ሁኔታ በሮማ ቤተክርስቲያን ውስጥ የነበሩ ምእመናን እና አንዳንድ ካህናት እንዱሁም መነኮሳት በቤተክርሰቲያኗ ያለውን የሥርዓትና የመሠረተ እምነት ብልሹነት እና አላግባብነት እንዱሁም የጳጳሳቱን የቅንጦት ኑሮ እና የመመለክ አባዜ በመመልከት በተላያየ ጊዜ ከቤተክርስቲያኗ እየተገነጠሉ እነርሱ የመሰላቸውን ሌላ ‘ሐይማኖት” እየደነገጉ ብዙ የጥፋት ልጆችን ልታፈራ ችላለች። በሰው እንጅ በመንፈስ ቅዱስ የምትመራ ባለመሆኗ አንድነቷን አስጠብቃ መቆየት ተሳናት።
ከሮማ ቤተክርስቲያን እንደ አሸን የፈሉ የምንፍቅና ጐራዎችን አወጣጥ በሚቀጥለው ክፍል እንመለከታለን።
…ይቀጥላል…

Wednesday, June 8, 2011

የቤተክርቲያን የመከራ ዘመናት - ዛሬስ ሰላም ነውን? (ክፍል አንድ)

በመጀመሪያ ደረጃ ዓለማቀፋዊት ቤተ ክርስቲያን ያሳለፈችውን የፈተና እና የመከራ ዘመናት ብንመለከት ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰውን ለማዳን በሥጋ በዚህ ዓለም በተገለጠ ጊዜ ሰይጣን እቡያን በሆኑ በአይሁድ ካህናት እና በፃፎችና ፈሪሳውያን ላይ አድሮ በእግዚአብሔር ቸርነት ለሕዝቡ ሁሉ ሲሰጥ የነበረውን የነፍስ ፈውስ የሆነውን የወንጌል ትምህርት እና የደዌ ሥጋ ፈውስ ደግሞ ተአምራቱን እነዲቃወሙ አደረጋቸው። እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ዓለሙን ሁሉ እንዲሁ በመውደዱ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የአይሁድ ምቀኝነትን ታግሶ ወንጌልን ሰብኮልን በዚህ ዓለም ኑሮው ምሳሌውን ትቶልን መርገመ ሥጋን እና መርገመ ነፍስን በጥምቀቱ እና በሞቶ ድል ነስቶልን በትንሳኤውም ትንሳኤ ሙታንን ተስፋ አስደርጎን ክብርት ቅድስት ድንግል እናቱን እናት አድርጎ ሰጥቶን በሐዋሪያት በኩል ለትውልደ ትውልድ የሚተላለፈውን ሥርዓቱን አስረክቦን በአርባኛው ቀን ወደ ሰማይ አረገ።
በዐረገ በአስረኛው ቀንም መቶ ሃያው ቤተሰብ በፅርሃ ፅዮን ተሰብስበው ሳለ መንፈስ ቅዱስ ተልኮ ሐዋሪያትና አርድዕትን በዚያ በማርቆስ እናት ቤት የተሰበሰቡትን ሁሉ የወንጌል ትምህርት ያስተምሩ ዘንድ የበቁ አደረጋቸው። ይህ ቀንም የቤተክርስቲያን የልደት ቀን ተብሎ ይጠራል።
ዓለም መድኃኒቷን ኢየሱስ ክርስቶስን እንዳልተቀበለችው ሁሉ ሐዋሪያትም በወንጌል ትምህርትን በሚያስፋፉበት እና በሚያስተምሩበት አገር ሁሉ ቀና መንገድ አልጠበቃቸውም። ትምህርታቸው በመጀመሪያ በቤተ አይሁድ የተጀመረ ሲሆን ለምቀኝነት እንቅልፍ የማይተኙት አይሁድ የክርስቲያን ማኅበርተኞችን ያገለግሉ ዘንድ ከተሾሙት መካከል ቀዳሜ ሰማእት ሊቀ ዲያቆናት ቅዱስ እስጢፋኖስን በድንጋይ ወግረው ገደሉት። በሌሎቹም ላይ እስራት ግርፋት እና መከራ አፀኑባቸው።
በዚህ ጊዜ የማኅበሩ አባላት በየቦታው ተሰደዱ። ነገር ግን እነዚህ የተበታተኑት ክርስቲያኖች በየሄዱበት ሁሉ የክርስትናን ትምህርት በደረሱበት ሁሉ አስፋፉት። በዚህ ጊዜም ወንጌል ትምህርት ለዓለም ተዳረሰች።
የቤተክርስቲያን ፈተና ከቤተ አይሁድ የሚመጣ ብቻ አልነበረም። ሐዋሪያት አርድእት እና ሐዋሪያነ አበው በተለያዩ የዓለም ከተሞች እየተዘዋወሩ ክርስትናን ሲያስፋፉ እና ወንጌልን ሲያስተምሩ ጣዖት አምላኪ የነበሩ አሕዛብ እና ዐላውያን ነገስታት በወንጌል መልእክተኞች ላይ ከፍተኛ እና አሰቃቂ የሆነ ስቃይ እና እንግልት አድርሰውባቸዋል። ለጣዖታቱ አገልጋይ የነበሩ ካህናት እና የአሕዛብ ነገስታት ከጣዖታት መስዋእት ከሚገኘው ገቢ የተጠቃሚነታቸው ተግዳሮት የነበረችውን እና ባዕድ አምልኮን እያወገዘች የሰበከችውን ቤተክርስቲያንን ለማጥፋት ደፋ ቀና አሉ። ከዘመነ ሐዋሪያት ንጉስ ቆስጠንጢኖስ እስከ ነገሰበት እስከ ፬ኛው መ/ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ድረስ ቤተክርስቲያን በዋሻ ከመሬት በታች ተወስና እስከ መኖር ያደረሳት ለህሊና እጅግ የሚዘገንን በክርቲያኖች ላይ አሰቃቂ ጭፍጨፋ እና ዘመቻ በተለያየ መልክ ተካሂዷል።
በዚህ ዘመን ከቤተ አይሁድ እና ከአሕዛብ ና ዐላውያን ነገስታት የሚመጣው ፈተና የቤተክርስቲያ የውጭ ፈተና ሲሆን ቤተክርስቲያን በወቅቱ ውስጣዊ ፈተናም ነበረባት። ከእነዚህም መካከል ከቤተ አይሁድ ወደ ክርስትና የተመለሱት ምእመናን እና ከአሕዛብ ወገን ወደ ክርስትና የተመለሱት ምእመናን መካከል የተፈጠረው ልዩነት ነው። ከቤተ አይሁድ የመጡት አሕዛብ ሳይገረዙ የቤተክርስቲያን ልጆች መሆን አይገባቸውም በሚል የተነሳው እና የቤተ አይሁድ እና የኦሪት ስርዐት ለማስቀጠል የነበራቸውን ሐሳብ ከአሕዛብ ወገን ወደ ክርስትና የተመለሱት ምእመናን በመቃወማቸው የከረረ ልዩነት ተፈጥሮ ነበር። ይህም በሐዋሪያት የመጀመሪያው ሲኖዶስ እልባት ያገኘ ሲሆን ከቤተ አይሁድ የተመለሱት ብዙዎቹ ይህንን የሐዋሪያት ውሳኔ በመቃዎም ከክርስትና የወጡ ነበሩ።
ከዚህ በተጨማሪም የግሪክ የጥንት ፍልስፍና ይዘው የገቡ አንዳድ ወገኖች መዳን በእዉቀት ነው በማለት ግኖስቲዝም የሚባል ይክርስትና ትምህርትን ከግሪክ ፍልስፍና ጋር ያጣመረ አስተሳሰብ ይዘው ብቅ ማለት ሌላው የቤተ ክርስትያን ፈተና ነበር
ቤተ ክርስቲያን የተላዩ ውጫዊ እና ውስጣዊ ፈተናዎችን አሳልፋ ከንጉስ ቆስጠንጢኖስ ዘመን ስትደርስ በአንፃራዊነት ከውጫዊ ፈተና ፋታ ያገኘችበት እና የቤተ ክርስቲያን ሰላማዊ ዘመን ነበር። በዚህ ዘመን ቤተክርስቲያን ከመንግስት ግብር ነጻ የሆነችበት እና ምእመናን በይፋ ክርስቲያናዊ የአምልኮ ስርዐታቸውን በነጻነት ማከናወን የቻሉበት ዘመን ነበር።
በዚህ ዘመን ቤተክርስቲያን ውጫዊ ሰላም ብታገኝም ውስጣዊ ፈተናዋ ግን በሰይጣን አቀናባሪነት መልኩን ለውጦ እጅግ በረቀቀ መንገድ ኑፋቄን ይዞ ብቅ አለ። አርዮስ በጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የባህርይ አምላክነት ላይ ጥርጥር የሚነዛ ትምህርትን በማስተማር እና በግጥም እና በሌሎች የሥነ-ጽሑፍ መንገዶች በየመንገዱ እና በየአገኘው አጋጣሚ ውሃ ለሚቀዱ ወይዛዝርት እና ቆነጃጅት እንዱሁም ከብት ለሚያግዱ ወጣቶች ህፃናት እና ገበሬዎች ሁሉ እያነበበ እሳስነበበ እንዱሁም በልዩ ልዩ ዜማ እያዜመ የኑፋቄ ትምህርቱን እየነዛ ቤተክርስቲያንን መበጥበጥ ጀመረ። በሦስቱ ምእት ሊቃውንት እና ቅዱሳን አባቶች በጉባኤ ኒቂያ ተመክሮ አልመለስም በማለቱ ተወግዞ ቢለይም ተከታዮቹ ቤተክርቲያንን እንቅልፍ ነስተዋት በቅዱሳን አባቶቻችን ላይ ብዙ መከራ አጽንተውባቸዋል።
የአርዮስ ኑፋቄ በኒቂያ ጉባኤ ተወግዞ ቢለይም ሌሎች አርዮስን ምሳሌ ያደረጉ ልዩ ልዩ የኑፋቄ ሰዎች እርሱን ተከትለው በምስጢረ ስጋዌ እና በመንፈስ ቅዱስ ህልውና ላይ የጥርጥር ትምህርት አስነስተው በተለያዩ ጉባኤዎች አባቶቻችን መክረው አልመለስም በማለታቸው በአንድ ቃል አውግዘው ለይተዋቸዋል። ቤተክርስቲያን እነዚህን መናፍቃን ለማውገዝ እና ሐይማኖትን መሰረት ለመወሰን ያደረገቻቸው ጉባኤያት (ጉባኤ ኒቂያ - አርዮስን ለማውገዝ ጉባኤ ቁስጢንጢንያ - መቅዶንዮስን ለማውገዝ እና ጉባኤ ኤፌሶን - ንስጥሮስን ለማውገዝ) ናቸው። በእነዚህ ጉባኤያት መናፍቃኑን አውግዘው የሐይማኖት መሰረት የሆነውን ጸሎተ ሐይማኖትን ሰርተውልን አልፈዋል።

...ይቀጥላል...

Wednesday, June 1, 2011

ሰው በምድር ሲኖር ሊያተርፍ የሚያቅደው ምንድ ነው?

እነሆ እኔነቴ እና እኔ በየቀኑ በሚኖረን የህይወት ተቃርኖ ጊዜ ሁልዜ አንድ ጥያቄ በአእምሮዬ ይመጣል። ይኸውም ”ሰው በምድር ሲኖር ሊያተርፍ የሚያቅደው ምንድ ነው?‘ የሚል ነው። የማቅደው እና ያቀድኩትን ለማግኘት የማደርገው እየተለያየብኝ።

ሰው በህይወት ዘመኑ ለህይወቱ ጠቃሚ መሆኑን ለይቶ ያልተረዳውን ጠቃሚውንም ጐጅውንም እንዲኖረው ይመኛል፤ ይፀልያልም። ነገር ግን እነዚህን ሁሉ ነገሮች እንዲኖሩት የሚሻው ለምን እንደሆነ ሲጠየቅ የሚመልሰው መልስ ሁልጊዜ ይገርማል።
ለምሳሌ አንድ ሰው እጅግ ባለፀጋ ሌላው ደግሞ ፈላጭ ቆራጭ መሪ አንዱ ደግሞ እጅግ ሊቅ እና እርሱ የደረሰበት የእውቀት ደረጃ ሌላ የማይደርስበት እና የዓለም ህልውና በእርሱ ክሂሎት እና እውቀት ጥገኛ ወዘተርፈ ሊሆን ይችላል።
ለምን ይህንን እንዲኖርህ ወደድክ ተብሎ ሲጠየቅ በምድር ላይ ጤናማ ደስተኛ እና ምቾት ያለው ህይወት መኖር እንደሚፈልግ እና እነዚህ ነገሮች እርሱ ለእነዚህ ጉዳዮች ማሟያ እንደሚጠቀምባቸው ሳያቅማማ ይናገራል።
ነገር ግን የጤናማ ህይወት ምንጭ ምንድነው? ገንዘብ ነውን? ወይስ ፈላጭ ቆራጭነት ነውን? ወይስ እውቀት ነውን?
የደስታ ምንጭስ ወዴት ነው? ገንዘብ ደስታ ይሆናልን? ስልጣንስ ደስታ ሆይ ወደ እኔ ና! ይለው ዘንድ ይችላልን? ወይስ እውቀት ደስታን በፋብሪካ ሊያመርተው ይችላልን?
የምቾትስ መገኛ ምንድነው? ገንዘብ ወይስ አዛዥነት ወይስ እውቀት?
እነዚህ ደስታ፥ጤናማነት እና ምቾት ምንድናቸው? መገኛቸውስ ምንድነው?
ልዑል እግዚአብሔር ሰውን ሲፈጥር ሰባት ባህሪያት እንዲኖሩት አድርጎ ነው የፈጠረው። ” ወይቤ ፡ እግዚአብሔር ፡ ንግበር ፡ ሰብአ ፡ በአርአያነ ፡ ወበአምሳሊነ - እግዚአብሔርም፡አለ፦ሰውን፡በመልካችን፡እንደ፡ምሳሌአችን፡እንፍጠር ‘ ዘፍ. ፩፥፳፮ ተብሎ እንደተፃፈ።
አራት ባህሪያተ ሥጋ እና ሦስቱ ባህሪያተ ነፍስ አሉት። አራቱ ባህሪያተ ሥጋ እንስሳትን ሲያስመስሉት ሦስቱ ባህሪያተ ነፍስ ደግሞ ፈጣሪውን እግዚአብሔርን ያስመስለዋል። ስለዚህ ደስታ ጤናማነት እና ምቾትን ስናስብ ሰው ሁለት ዓይነት ደስታ ጤናማነት እና ምቾትን እናገኛለን። ስጋዊ እና ነፍሳዊ።
የሰው የማስታወስ እና የመናገር የማመዛዘን ችሎታ ከነፍስ ባህሪያት የተገኙ በመሆናቸው ስጋዊ ደስታ ጤናማነት እና ምቾት የስጋ ስሜቶች በመሆናቸው እነዚህ ሲጐድሉ ተመለሶ መጎሳቆሉ አይቀሬ ነው። ለምሳሌ አንድ ሰው በብርድ ጊዜ የብርድ መከላከያ እና ምቾት ያላቸው በውድ ዋጋ የተገዙ አልባሳትን ቢለብስ እና ከጥቂት ጊዜ በኋላ ቢራቆት ቀደም ብሎ የለበሰውን ልብስ በማስታወስ መፅናናት ይሳነዋል። ይህ ልብስ የፈጠረው ጊዜያዊ ስሜት ከልብሱ መውለቅ ጋር አብሮ ይጠፋል። ሌሎችም ቁሳዊ በሆኑ ነገሮች ለሰውነታችን የምናደርጋቸው ተግባራት ዘላለማዊ የሆነ ምቾት ደስታ እና ጤናማነት ሊፈጥሩልን አይቻላቸውም።
ሰው ከሌሎች እንስሳት ተለይቶ መናገር (ነባቢነት) ማመዛዘን (ልባዊነት) እና ዘላለማዊ ህይወት (ህያውነት) አለው። በእነዚህ በሦስቱ ባህሪያተ ነፍስ አምላኩ ይመስላል፤ በምድር በስባሽ ፈራሽም ሆኖ አይቀርም። ስለዚህ በእነዚህ በባህሪያተ ነፍሳችን ልንረዳው የምንችለው ነገር ሁሉ ዘላለማዊ ሀብታችን እና ትርፋችን ነው። እንግዲህ እውነተኛ ጤናማነት ደስተኝነት እና ምቾት ከየት ይገኛሉ የሚለውን መሰረታዊ ጥያቄ እነዚህን ነገሮች በባህሪያተ ነፍሳችን እንዴት መረዳት እና ለባህሪያተ ነፍሳችን ገንዘብ ማድረግ እንችላለን ወደሚል ጥያቄ መቀልበስ እንችላለን። ምክንያቱም በነፍስ ባህሪያት ልንገነዘበው እና ልናጣጥመው የምንችለው ነገር ለዘለቄታው አብሮን የሚኖር በመሆኑ ነው።
ለምሳሌ ደስተኝነትን እንመልከት። አንድ ሰው ደስታን በቁሳዊ ነገሮች በገንዘብ እና በመሳሰሉት ነገሮች ማግኘት አይችልም። ቢገኝም ስጋዊ ባህሪያችን ብቻ የሚያጣጥመው ያ አስገኚው ሲጠፋ አብሮ የሚጠፋ ጊዜያዊ ስሜት ብቻ ነው የሚሆነው። ነገር ግን አንድ ሰው በአእምሮው ውስጥ ደስታ እና እርካታን የሚፈጥረው መልካም ሀሳብን ለአእምሮው ሲመግበው ነው። መልካም ሀሳብ እና መልካም ሥራ የአእምሮ ምግቦች ናቸው። እነዚህ መልካም ሀሳቦች እና ሥራዎች የሚገኙት ደግሞ ለሰው ሁሉ ቅን እና ደግ በመሆን ነው። ቅንነት እና ደግነት ደግሞ ከፍቅር የሚመነጩ ናቸው። ለማይወደድ ሰው ቅን እና ደግ መሆን ከቶ ከባድ ነው።
አንድ ሰው ሁልጊዜ አብሮት የሚኖር የልብ መረጋጋት እና ደስታን ገንዘብ ለማድረግ ሰውን ሁሉ እንዲሁ መውደድ ነው። ጠላቱን እንደራሱ አድርጎ የሚወድ ልብ ደስታ ዘላለማዊ ነው። በራሱ ላይ ባለድል ነውና። ሰውን ሁሉ ለመውደድ እራስን ማሸነፍ ትህትናን መልመድ እና መንፈሳዊ አባቶቻችን ታሪክ እኛም እንደ አቅማችን መለማመድ ያስፈልገናል።
ሰው ለባዊ ፍጡር በመሆኑ ከራሱ ስህተት የተነሳ የሚመጣበትን የአእምሮው ትችት መሸሽ ከቶ አይቻለውም። እግዚአብሔር እኛን ለባዊ አድርጎ ሲፈጥረን አእምሮን ያህል ርቱዕ ዳኛ በላያችን ሾሞብናል። እናም በጨለማ ተጋርዶ በስውር መጥፎ ሥራ በመስራት ብዙ ሀብት ብናፈራ በሰዎች ላይም ግፍ ብናበዛ ከእግዚአብሔር እና ከአእምሯችን ልናመልጥ አይቻለንም። ስለሆነም ሞልቶ በተረፈው ቤታችን ብቸኛ ሐዘንተኛ እንሆናለን።
ሌሎች የህይወት እሴቶችም ከዚህ ተለይተው የሚታዩ አይደሉም። ለስጋ ብቻ የሚመች ነገር ግን ለባህሪያዊ ነፍሳችን የማይመች ስራ ብንሰራ ስጋ የተደረገለትን ሁሉ በአጭር ጊዜ ረስቶ ለነፍስ ወቀሳ አሳልፎ ይሰጠናል። ምቾትም ሆነ ጤናማነት ሁሉም ከልብ ይመነጫሉ። በጐ ሥራ በመስራት በልቡ ሀሴት የሞላ ሰው አስጨናቂ ጉዳይ የለበትም። ጭንቀት ከሌለበት ደግሞ ሙሉ ሰውነቱ ጤናማ ይሆናል። ጤናማ ሰውነት ደግሞ ሁልጊዜ ምቾት ይሰማዋል። ”እነደ ንፁህ ህሊና የሚመች ትራስ አይገኝም!‘ አይደል የሚሉት አበው። ምንም ጥርጥር የለውም፤ ውስጣዊ ሰላም ከአፍኣ (ውጫዊ) ምቾት እጅጉን ይበልጣል። ምክንያቱ ደግሞ አፍአዊ ደስታን በስጋችን ውስጣዊ ደስታችንን ደግሞ በልባችን (በነፍሳችን) እንገነዘበዋለንና ነው።
እንግዲህ አንባቢ ሆይ! በምድራዊ ህይወትህ/ሽ ደስታን ምቾትን ጤናማነት እና የህሊና እርካታን ለማትረፍ ካቀድህ/ሽ የሚከተሉትን መመሪያዎች ተግብር/ሪ፦
፩ኛ. ፈጣሪህ/ሽ እግዚአብሔርን ውደደው/ጂው፤ ባለህ/ሽ ጊዜ ሁሉ እርሱ የሰውን ልጅ ለማዳን ብሎ የከፈለውን መስዋእትነት እና ላንተ/ቺ ያለውን ፍቅር አስብ/ቢ። በዙሪያህ/ሽ ያሉት በህይወት እንድትኖር/ሪ ያደረጉህ/ሽ ነገሮች ሁሉ የእርሱ ሀብቶች ሲሆኑ ያለምንም ዋጋ እንደሰጠህ/ሽ አስታውስ/ሽ።
፪ኛ.ሰውን ሁሉ እንዱሁ ውደደው/ጂው፤ አንተ/ቺ ለሰው ስለምታደርገው/ጊው ውለታ እና በጎ ሥራ አቅድ/ጅ እንጅ የማንኛውንም ሰው ስጦታ ተስፋ አታድርግ/ጊ። ስጦታውን ሳታገኝ ብትቀር/ሪ የኑሮህ/ሽ ዋጋ ምንጭ የሆነውን ለዚያ ሰው ያለህን/ሽን ፍቅር ያቀዘቅዝብሃልና/ብሻልና። በምንም ዓይነት መንገድ ለራስህ/ሽ አታዳላ/ይ።
፫ኛ. ቁሳዊ ነገሮችን አብዝተህ/ሽ አትመኝ፤ ከማንኛውም ሰው ወይም ከፈጣሪህ/ሽ ይልቅ ለእነዚህ ቁሳዊ ነገሮች የበለጠ ፍቅር እንዳይኖርህ/ሽ እራስህን/ሽን በየጊዜው መርምር።
፬ኛ. ሁል ጊዜ አእምሮህን/ሽን በማይጠቅም ሐሳብ እንዳይባዝን እራስህን/ሽን በጸሎት እና በሥራ ባተሌ አድርግ/ጊ። በተግባር የሚለወጥ ሐሳባ ቢኖርህ/ሽ በእቅድህ/ሽ ውስጥ ፃፈው እንጅ በበጐ አስጀምሮ የተከተልከው/ሽው ሐሳብ መንታው እየበዛ ህልም ከሚመስል ቅዠት ውስጥ እንዳያስገባህ/ሽ የሞት እናት የሆነውንም ሐጢያት ጣዕም አጉልቶ እንዳያሳይህ/ሽ።
፭ኛ. መንፈሳዊነት እንደ ክሂሎት የሚዳብር ነው፤ እናም ተለማመደው/ጂው። ቁጣን ለማስወገድ፥ ትሁት እና ታጋሽ ለመሆን፥ የአፍህ/ሽ ቃላት ቅንነት እና መልካምነትን የሚያሰዩ ቁጣን የሚያበርዱ እንዲሆኑ፥ፍቅር እና ሌሎች የመንፈስ ፍሬዎች ገንዘብህ/ሽ እንዲሆኑ ተለማመድ/ጅ።
፮ኛ. ቅዱሳት መፃሕፍትን በየጊዜው አንብብ/ቢ፤ መልካም የሆነውን ሁሉ ለመረዳት ልብንም በሐይማኖት ለማቅናት ያስፈልጉሀልና/ሻልና። የዘነጋኸውን/ሽውን ለማስታወስ በቀዘቀዝክበት/ሽበት ነገር ለመነቃቃት ያገለግሉሃል/ሻል።
፯ኛ. ስንፍናን አስወግድ/ጅ፤ ለሥጋ ምግብነት የሚጠቅሙህ/ሽ እና በጐ ሥራ ለመስራት የሚያገለግሉህ/ሽ ነገሮችን ለማሟላት ተግተህ/ሽ ሥራ/ሪ። ነገር ግን ይህንን ምክንያት አስደርጐ የሚበልጥ ዋጋ እንዳያሳጣህ/ሽ ተጠንቀቅ/ቂ። ጸሎትህን/ሽን እንዳያታጉልብህ/ሽ፤ ከሌሎች ይልቅ ለራስህ/ሽ መድሎን እንዳያስደርግህ/ሽ፤ መልካም ሥራን እሰራለሁ አስብሎ መበደልን እንዳያስለምድህ/ሽ እራስህን/ሽን ጠብቀው/ቂው።
እንዲህ ያለ የፍቅር ህይወት ኖረህ/ሽ እየው/ይው። በህይወት ዘመንህ/ሽ ሁሉ ልታተርፈው/ፊው ያቀድኸውን/ሽውን ሁሉ ታገኛለህ/ሽ።